1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

ጀርመን ተገን ጠያቂዎችን ከድንበር መለሰች

እሑድ፣ ግንቦት 3 2017

ጀርመን ከአጎራባች የአውሮጳ ሀገራት ተሻግረው የመጡ 19 ተገን ጠያቂቂዎችን ጨምሮ በርካታ ስደተኞችን ከድንበሯ መለሰች ። ርምጃው በስደተኞች ጉዳይ ላይ ጠንከር ያለ አቋም እንዳለው የተነገረለት አዲሱ የጀርመን መንግስት የመጀመሪያው ነው ተብሏል።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4uF5S
Deutschland Guben 2025 | Bundespolizei kontrolliert Fahrzeuge an deutsch-polnischer Grenze
ምስል፦ John Macdougall/AFP/Getty Images

መራሄ መንግስት  ፍሬድሪክ ሜርስ  የሚመሩት አዲሱ መንግስት ስልጣን በተረከበ በሁለት ቀናት ውስጥ ጀርመን የምትዋሰንባቸው ድንበሮች ቁጥጥር  ሲያጠናክር በዚሁ የተገን ጥያቄ ያቀረቡ 19 ስደተኞች ጥያቄ ውድቅ መደረጉን ቢልድ አም ዞንታግ የተሰኘው የጀርመን ጋዜጣ ዘግቧል። 
ባለፉት የሀሙስ እና ዓርብ ቀናት ብቻ በሁሉም የድንበር አካባቢዎች ወደ ጀርመን ለመግባት ከሞከሩ 365 ሰነድ አልባ ስደተኞች እና ተገን ጠያቂዎች መካከል 19 ተገን ጠያቂዎችን ጨምሮ 305 ስደተኞች ጀርመን እንዳይገቡ ተከልክለዋል።
የተገን ጥያቄ ካቀረቡ ስደተኞች ውስጥ “ለጥቃት የተጋለጡ” ናቸው የተባሉ አራት ሰዎች ጥያቄያቸው ተቀባይነት አግኝቶ ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገቡ ተደርገዋል። 

የጀርመን ፖሊስ አንድ መኪና ሲያስቆም
ምስል፦ John Macdougall/AFP/Getty Images

የተገን ጠያቂዎች እና የስደተኞች ጥያቄ ውድቅ ለመደረጉ ህገ ወጥ ቪዛ እና የተጭበረበሩ የጉዞ ሰነዶች ይዘው በመገኘታቸው ነው ተብሏል። 
ጀርመን በሁለቱ ቀናት ጥብቅ የድንበር ቁጥጥሯ ተመላሽ ከተደረጉ ስደተኞች እና ተገን ጠያቂዎች በተጨማሪ 14 ህገ ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎችን በቁጥጥር አውላለች። በተጨማሪ በሌሎች 48 ሰዎች ላይ የመያዣ ትዕዛዝ መውጣቱን ያመለከተው ዘገባው የግራ ቀኝ እና የቀን አክራሪ አስተሳሰቦችን ጨምሮ አክራሪ የእስልምና አስተምሮ ይዘው ሲንቀሳቀሱ ነበር የተባሉ ዘጠኝ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ዘገባው አመልክቷል።