1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የጥር 26 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ጥር 26 2017

የዩጋንዳ አቻቸውን ለአፍሪቃ ዋንጫ ማጣሪያ የሚገጥሙት ሉሲዎቹ ከጅቡቲ ጋር የወዳጅነት ግጥሚያ ሊያደርጉ ነው ። ጅቡቲ በበርካታ ቡድኖች በርካታ ግብ አስተናግዶ አንድም ሳያስቆጥር የሚሸኝ ነው ። ቃለ መጠይቅ ይኖረናል ። የእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ እና የጀርመን ቡንደስሊጋ ውጤቶችንም አጠር አድርገን እናቀርባለን ።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4pyz2
የዩናይትድ ስቴትስ የሴቶች ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ተሰላፊ ትውልደ ኢትዮጵያዊት
የዩናይትድ ስቴትስ የሴቶች ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ተሰላፊ ትውልደ ኢትዮጵያዊት በዓለም ዋንጫ። ፎቶ ከማኅደርምስል፦ Abbie Parr/AP Photo/picture alliance

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

የኬንያ እና የሱዳን አትሌቶች የተሳተፉበት 42ኛው የጃንሜዳ ኢንተርናሽናል አገር አቋራጭ ሻምፒዮና በትናንትናው ዕለት ተከናውኗል አዲስ አበባ ውስጥ ። የዩጋንዳ አቻቸውን ለአፍሪቃ ዋንጫ ማጣሪያ የሚገጥሙት ሉሲዎቹ ከጅቡቲ ጋር የወዳጅነት ግጥሚያ ሊያደርጉ ነው ። ቃለ መጠይቅ ይኖረናል ። የእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ እና የጀርመን ቡንደስሊጋ ውጤቶችንም አጠር አድርገን እናቀርባለን ።

አትሌቲክስ

4 ሚሊዮን ብር በጀት የተመደበለት 42ኛው የጃንሜዳ ኢንተርናሽናል አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ትናንት አዲስ አበባ ውስጥ ተከናወነ ። በወንድ እና በሴት የ6፣ የ8 እና የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድሮች እንዲሁም የድብልቅ ሪሌ ፉክክር መከናወኑም ተጠቅሷል ። በውድድሩ ከክልሎች፣ የከተማ አስተዳደሮች፣ ቡድኖች እና የአትሌቲክስ ማሰልጠኛ ማዕከላት በተጨማሪ ከኬንያ እና ከሱዳን ሁለት ሁለት አትሌቶች ተሳታፊ እንደነበሩም ተዘግቧል ።

የውድድሩ ዓላማ በዋናነት አትሌቶች በአገር ውስጥ የውድድር እድል እንዲያገኙ ለማድረግ መሆኑም ተገልጧል ። የተለያዩ አትሌቶችን ከተለያዩ ዘርፎች በማሳተፍ የእርስ በእርስ የልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉ እድል መፍጠርም ዋነኛ ግቡ እንደነበር ተጠቁሟል ።  በውድድሩ አሸናፊ ለሆኑ አትሌቶች በአጠቃላይ የ865,000 ብር የማበረታቻ ሽልማት መሰጠቱንም አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ዘግቧል ። ደረጃቸውን የጠበቁ የመወዳደሪያ ስፍራዎች በበቂ በሌሉበት ሁኔታ መሰል ውድድሮች ጠቀሜታቸው ላቅ ያለ ነው።  በኢትዮጵያ በዋናነት የመሮጫ ቦታዎች እጥረት ብርቱ ፈተና መሆኑ በተደጋጋሚ ይነገራል ።  የጥር 19 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

እግር ኳስ

በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ማንቸስተር ሲቲ ትናንት በአርሰናል 5 ለ1 ጉድ ሁኗል ። ለማንቸስተር ሲቲ የማጽናኛዋን ብቸና ግብ ኧርሊንግ ኦላንድ አስቆጥሯል ። ጨዋታው በተጀመረ 2ኛ ደቂቃ ላይ በማርቲን ኦዴጋርድ ማግባት የጀመረው አርሰናል መደበኛው 90 ደቂቃ ተጠናቆ በጭማሪው ሦስተኛ ደቂቃ ጭምር ተከታታይ ግቦችን ሲያስቆጥር ነበር ። ቶማስ ፓርቴይ፣ ማይለስ ሌዊስ እና ካይ ሐቫርትስ እንዲሁም ኤታን ንዋኔሪ አምስቱን ግቦች በተከታታይ በማስቆጠር ማንቸስተር ሲቲን ኩም አድርገዋል ። አርሰናል በደረጃ ሰንጠረዡም 50 ነጥብ ሰብስቦ ሁለተኛ መሆን ችሏል ። 

 የማንቸስተር ሲቲ አጥቂ ኧርሊንግ ኦላንድ
በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ በአርሰናል 5 ለ1 ጉድ ለሆነው ማንቸስተር ሲቲ ብቸኛዋን ግብ ያስቆጠረው ኧርሊንግ ኦላንድ ከብሬንትፎርድ ጋር ሲጫወት ። ፎቶ ከማኅደርምስል፦ IMAGO/Action Plus

ቅዳሜ ዕለት በርመስን በሜዳው 2 ለ0 አሸንፎ የተመለሰው መሪው ሊቨርፑል አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረውም አርሰናልን በስድስት ነጥብ ይበልጣል ። 56 ነጥብ አለው ።  ብራይተንን የግብ ጎተራ አድርጎ 7 ለ0 ያበራየው ኖቲንግሀም ፎረስት በ47 ነጥብ ሦስተኛ ነው ። ማንቸስተር ሲቲ 41 ነጥቡ ላይ ተወስኖ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ።  ማንቸስተር ዩናይትድ በሜዳው ኦልድ ትራፎርድ ክሪስታል ፓላስን ትናንት አስተናግዶ የ2ለ0 ሽንፈት ገጥሞታል ። በ29 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ይዋዥቃል ።  ላይስተር ሲቲ፣ ኢፕስዊች ታወን እና ሳውዝሐምፕተን ከ18ኛ እስከ 20ና ወራጅ ቀጣና ውስጥ ይገኛሉ ። የጥር 12 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ቡንደስሊጋ

በጀርመን ቡንደስሊጋ መሪው ባዬርን ሙይንሽን ትናንት ሆልሽታሽን ኪዬልን 4 ለ3 አሸንፎ ነጥቡን 51  በማድረስ በመሪነት እየገሰገሰ ነው ። ባዬርን ሌቨርኩሰን በ45 ይከተላል ። ትናንት አንድ ተጨዋቹ በቀይ ካርድ ከሜዳ ቢሰናበትበትም ሆፈንሀይምን 3 ለ1 ድል አድርጓል ። ከቮልፍስቡርግ ጋር ትናንት አንድ እኩል የተለያየው አይንትራኅት ፍራንክፉርት በቡንደስሊጋ የደረጃ ሰንጠረዡ ሦስተኛ ላይ ይገኛል፥  38 ነጥብ አለው ። ላይፕትሲሽ በ33 ነጥብ አራተኛ ነው፥ ቅዳሜ ዕለት ከዑኒዮን ቤርሊን ጋር ያለምንም ግብ ተለያይቷል ። ሐይደንሀይም፣ ሆልሽታየን ኪዬል እንዲሁም ቦሁም ከ16ኛ እስከ 18ኛ ወራጅ ቀጣና ውስጥ ተደርድረዋል ።

በቡንደስሊጋው ሳንክት ፓውሊ እና ዑኒዮን ቤርሊን ቡድን ተጨዋቾች
በቡንደስሊጋው ሳንክት ፓውሊ እና ዑኒዮን ቤርሊን ቡድን ተጨዋቾች ምስል፦ Christian Charisius/dpa/picture alliance

ሉሲዎች

የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን (ሉሲዎቹ) በቀጣይ ሳምንታት ውስጥ ከጎረቤት ጅቡቲ ጋር የወዳጅነት ከኡጋንዳ ብሔራዊ ቡድን ደግሞ ለአፍሪቃ ዋንጫ ማጣሪያ ይጋጠማል ።

በአፍሪቃ አገራት የሴቶች እግር ኳስ ዋንጫ (WAFCON) የማጣሪያ የመጀመርያ ዙር የደርሶ መልስ ግጥሚያዎቹ የካቲት ወር ውስጥ ይከናወናሉ ። የመጀመሪያው የማጣሪያ ጨዋታ ከመከናወኑ በፊት የፊታችን ረቡዕ ሳምንት (የካቲት 5 ቀን፣ 2017 ዓ.ም) ሉሲዎች ከጅቡቲ ጋር አዲስ አበባ ውስጥ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም የወዳጅነት ግጥሚያ ያከናውናሉ ። የመልሱ ጨዋታም የካቲት 9 ቀን እዛው አበበ ቢቂላ ስታዲየም ሊከናወን ቀጠሮ ተይዟል ።

የጅቡቲ ቡድን በዓለም አቀፍ መድረክ ከዚህ ቀደም ባደረጋቸው ግጥሚያዎች ያለፉትን ስድስት ግጥሚያዎች ብንመለከት በሁሉም አንዲትም ግብ ሳያስቆጥር በሰፋ ግብ ነበር የተሸነፈው ። በሩዋንዳ የ2 ለ0፤ በብሩንዲ የ3 ለ0፤ በዩጋንዳ የ5 ለ0 እንዲሁም በቶጎ የ6 ለ0 እና 7 ለ0 በደርሶ መልስ የ13 ለ0 ግብ መሸነፉ ይታወሳል ።

የጅቡቲ ቡድን ከሉሲዎቹ ጋር ካደረጋቸው ግጥሚያዎች ከአምስት ዓመት በፊት ለአፍሪቃ ዋንጫ ማጣሪያ 8 ለ0 በደርሶ መልስ 10 ለ0 ያሸነፉበት ከፍተኛው ነው ። በአንጻሩ የአፍሪቃ ዋንጫ ማጣሪያ ተጋጣሚው የዩጋንዳ ቡድን ከሉሲዎቹ ጋር ተገዳዳሪ መሆኑ ይታወቃል ። ለአዲሱ የሉሲዎች አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ ከጅቡቲ ጋር የተዘጋጀው የወዳጅነት ግጥሚያ ምን የሚፈይደው ነገር ይኖራል? የስፖርት ጋዜጠኛ ዖምና ታደለ ። 

 የስፖርት ጋዜጠኛ ዖምና ታደለ ።
የስፖርት ጋዜጠኛ ዖምና ታደለ ።ምስል፦ privat

ሉሲዎቹ ከዩጋንዳ ጋር የሚያደርጓቸው የደርሶ መልስ የአፍሪቃ ዋንጫ የማጣሪያ የመጀመሪያ ዙር ጨዋታዎች ደግሞ ለካቲት 14 እና 19 ቀጠሮ ተይዞባቸዋል ። ዩጋንዳ በአንጻሩ በአፍሪቃ የሴቶች እግር ኳስ ታሪክ ጠንካራ የሚባል ቡድን ነው ። የዛሬ ሁለት ዓመት ከስምንት ወር ከሉሲዎቹ ጋር ባደረገው ዓለም አቀፍ የወዳጅነት ግጥሚያ የኡጋንዳ ቡድን በደርሶ መልስ 1 ለ0 ማሸነፉ ይታወሳል ። ሁለቱ ቡድኖች ለአፍሪቃ ዋንጫ ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ስድስት ግጥሚያዎች፦ ኢትዮጵያ ኡጋንዳን ሦስት ጊዜ አሸንፋ አንድ ጊዜ አቻ ወጥታለች ። ኡጋንዳ ኢትዮጵያን ሁለት ጊዜ አሸንፋ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይታለች ። የዩጋንዳ ቡድን የቅርብ ጊዜ እንቅስቃሴው ጠንከር ያለ ከመሆኑ አንጻርስ አሰልጣኙ ምን ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል? የጥር 5 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የዩናይትድ ስቴትስ የሴቶች ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድ ተከላካይ ናኦሚ ግርማ

ናኦሚ ግርማ (4 ቁጥር መለያ የለበሰችው)
ናኦሚ ግርማ (4 ቁጥር መለያ የለበሰችው) የዩናይትድ ስቴትስ የሴቶች ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ከስዊድን ጋር በተጋጠመበት ወቅት ። ፎቶ ከማኅደርምስል፦ Jenna Watson/USA TODAY Network/IMAGO

ናኦሚ ግርማ  የዩናይትድ ስቴትስ  የሴቶች ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ውስጥ በመግባት የመጀመሪያዋ ትውልደ ኢትዮጵያዊት መሆን ችላለች ። ምንም እንኳን ሳን ሆዜ ካሊፎርኒያ ተወልዳ ብታድግም ከእንግሊዝኛ ባሻገር አማርኛም የምትናገረው ናኦሚ ኳስ የጀመረችው በአባቷ የተነሳ ነው ሲል ቢቢሲ ዘግቧል ። አባቷ «ማለዳ ሶከር» በሚል ሳን ሆዜ ውስጥ ባቋቋሙት ቡድንም ናኦሚ የኳስ ሕይወቷን ሀ ብላ በመጀመር በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተመራጭ መሆን ችላለች ። «ማለዳ ሶከር» የተቋቋመው ኢትዮጵያውያን ልጆች እንዲገናኙበት ለማድረግ እንደነበረም ተዘግቧል ። አባቷ አቶ ግርማ ዐወቅ ወደ ዩናይትድ ስቴትስ የተሰደዱት ጦርነትን በመሸሽ፤ እናቷ ወ/ሮ ሠብለ ደምሴ ደግሞ ለትምህርት እንደነበር ቢቢሲ አክሎ ዘግቧል ።

ናኦሚ በሴቶች የእግር ኳስ ታሪክ ከዚህ ቀደም የነበረውን የዝውውር ክፍያ ክብረ ወሰን መስበርም ችላለች ።  በአንድ ሚሊዮን ዶላር ከዩናይትድ ስቴትስ ሳና ዲዬጎ ዌቭ ቡድን ወደ እንግሊዙ ቸልሲ ቡድን የተዘዋወረችው ናኦሚ የዓለማችን ምርጥ ተከላካይ መሆኗም ተዘግቧል ። ከዚህ ቀደም ከፍተኛው የዝውውር ክፍያ 866,000 ዶላር ነበር ። ክፍያውም በቤይ ኤፍ ሲ ቡድን ለማድሪድ የተፈጸመው የዛምቢያዋ አጥቂ ራቼል ኩንዳናንጂን ባለፈው ዓመት ለማስመጣት ነበር ። 

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ነጋሽ መሐመድ

 

ማንተጋፍቶት ስለሺ ሥዩም Mantegaftot Sileshi ዜና አዘጋጅ፤ መርኃ ግብር መሪ፤ የሳምንታዊ ስፖርት አዘጋጅ ነው፥ በአጭር ፊልም የበርካታ ዓለም አቀፍ ተሸላሚው ማንተጋፍቶት የቪዲዮ ዘገባዎችንም ያዘጋጃል።@manti