1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የግንቦት 4 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ግንቦት 4 2017

ሪያል ማድሪድ ትናንት ሲመራ ቆይቶ የማታ ማታ በባርሴሎና ሽንፈት ገጥሞታል ። በኮፓ ደ ሬይ ዋንጫ የወሰደው ባርሴሎና ለላሊጋው ዋንጫም እየገሰገሰ ነው ። የባዬርን ሙይንሽን የረዥም ዘመን ተጨዋች ቶማስ ሙይለር ከቡድኑ ስንብት ተደርጎለታል ። አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ ከባዬር ሌቨርኩሰን መለየቱን ይፋ አድርጓል፤ ሪያል ማድሪድ ይጠብቀዋል ።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4uHNJ
በኮፓ ደ ሬይ ዋንጫ የወሰደው ባርሴሎና ለላሊጋው ዋንጫም እየገሰገሰ ነው
በዘንድሮ የኮፓ ደ ሬይ የፍጻሜ ግጥሚያ ሪያል ማድሪድን አሸንፎ ዋንጫ የወሰደው ባርሴሎና ለላሊጋው ዋንጫም እየገሰገሰ ነው ምስል፦ Borja Suarez/REUTERS

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

ሪያል ማድሪድ ትናንት ሲመራ ቆይቶ የማታ ማታ በባርሴሎና ሽንፈት ገጥሞታል ። ባርሴሎና ዋንጫ የማንሳት እድሉን እጅግ ከፍ አድርጓል ። የባዬርን ሙይንሽን የረዥም ዘመን ተጨዋች ቶማስ ሙይለር ከቡድኑ ስንብት ተደርጎለታል ።  አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ ከባዬር ሌቨርኩሰን መለየቱን ይፋ አድርጓል፤ ሪያል ማድሪድ ይጠብቀዋል ። 

54ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተጠናቅቋል

ከሚያዝያ 28 እስከ ግንቦት 03 ቀን፣ 2017 ዓ.ም በኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ሲከናወን የቆየው 54ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ትናንት ተጠናቅቋል ። በወንድ እና ሴት የፍጻሜ ውድድር ከተካሄደባቸው መካከል፦ የ5000፤ የ1500 እንዲሁም የ100 ሜትር በአራት የዱላ ቅብብል ይገኝበታል ።

በአጠቃላይ ውድድሩ 1,379 አትሌቶች፣ 31 ቡድኖች እና ተቋማት እንዲሁም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች መሳተፋቸው ተገልጧል ። ለአንድ ሳምንት ግድም በተከናወነው 54ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ውድድር በድምር ውጤት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 279 ነጥብ በማምጣት በአንደኛነት አሸንፏል ። መቻል 242 ነጥብ በመሰብሰብ ሁለተኛ ደረጃ ሲያገኝ፤ ሸገር ሲቲ በ143 ነጥብ ሦስተኛ ደረጃ አግኝቷል ።

በስፔን ላሊጋ ሪያል ማድሪድበ ባርሴሎና ዳግም ጉድ ሆነ

በስፔን ላሊጋ ባርሴሎና ትናንት ሪያል ማድሪድን 4 ለ3 በመርታት የደረጃ መሪነቱን ይበልጥ አጠናክሯል ። በትናንቱ ግጥሚያ ቀዳሚውን ግብ በተገኘ ፍጹም ቅጣት ምት 5ኛ ደቂቃ ላይ ከመረብ ያሳረፈው የሪያል ማድሪዱ አጥቂ ኪሊያን እምባፔ ነበር ።  ከጥቂት ቆይታ በኋላ በ14ኛው ደቂቃ ላይ ይኸው ግብ አዳኝ ኪሊያን እምባፔ ሁለተኛውን ግብ በማስቆጠር ባርሴሎናን በገዛ ሜዳው እና በደጋፊው ፊት አስደንግጦ ነበር ። ሁለተኛው ግብ እንድትቆጠር ቪንሰንት ጁኒዬር በድንቅ ሁኔታ ከተከላካዮች እግር ፊት አስቀድሞ ኳሷን ለኬሊያን እምባፔ በመላክ ብቃቱን ዐሳይቷል ።

 ኬሊያን እምባፔ 3 ግብ ለሪያል ማድሪድ በማስቆጠር ሔትትሪክ ሠርቷል
ኬሊያን እምባፔ እንደለመደው ሦስት ግቦችን ለሪያል ማድሪድ በማስቆጠር ሔትትሪክ ሠርቷልምስል፦ Manu Fernandez/AP Photo/picture alliance

በ19ኛው ደቂቃ ባርሴሎና ያገኘውን የማእዘን ምት ኤሪክ ጋርሺያ በጭንቅላት ገጭቶ ከመረብ አሳርፏል ። በገዛ ሜዳቸው ግራ ተጋብተው የነበሩት የባርሴሎና ደጋፊዎችን እፎይ ያስባለች እና ያነቃቃች ግብ ። ከተከላካዮች ዕይታ ውጪ ከግቡ በስተግራ ቆሞ አጋጣሚውን ሲጠብቅ የነበረው ላሚን ያማል 32ኛው ደቂቃ ላይ ባርሴሎናን አቻ ያደረገውን ግብ ተረጋግቶ አስቆጥሯል ። ሰባት የሪያል ማድሪድ ተጨዋቾች ፍጹም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ ተደርድረው ሌሎች ተጨዋቾች ላይ ትኩረት ባደረጉበት ቅጽበት ለብቻው ነጠል ብሎ የነበረው ላሚን ጉድ አድርጓቸዋል ። የሚያዝያ 27 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ጨዋታው ተጋግሎ 34ኛ ደቂቃ ላይ ራፊና ዲያስ 3ኛውን ግብ ከመረብ በማሳረፍ ባርሴሎናን ቀደሚ አድርጓል ። ይኸው ራፊና 41ኛው ደቂቃ ላይም የተሻማ ኳስ በጭንቅላት በመግጨት ለጥቂት ከግቡ አግዳሚ በላይ በማለፍ ግብ ሳይሆን ቀርቷል ።  በፈጣን እንቅስቃሴው የሪያል ማድሪድ ተከላካዮችን ሲያስጨንቅ የቆየው ራፊና 45ኛው ደቂቃ ላይ ግን ተሳክቶለት ለራሱ ሁለተኛ ለባርሴሎና የማሸነፊያዋን አራተኛ ግብ ከመረብ አሳርፏል ።

የባርሴሎና እና ሪያል ማድሪድ ፍጥጫ አሁንም ቀጥሏል

መደበኛው 45 ደቂቃ ተጠናቅቆ በጭማሪው 8ኛ ደቂቃ ላይ እምባፔ ለሪያል ማድሪድ ቢያስቆጥርም ግቡ ከጨዋታ ውጪ ተብሏል ። ወዲያውም ባርሴሎና 4 ለ2 እየመራ የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቅቆ ረፍት አድርገዋል ። ከረፍት መልስ 52ኛው ደቂቃ ላይ ላሚን ያማል ሪያል ማድሪድን ያስደነገጠ ግብ ቢያስቆጥርም ለጥቂት ከጨዋታ ውጪ ተብሎ ተሽሮበታል ።  70ኛ ደቂቃ ላይ ቪንሰንት ጁኒዬር በድንቅ ሁኔታ ያቀበለውን ኳስ ኪሊያን እምባፔ 3ኛ ግብ ለሪያል ማድሪድ በማስቆጠር ሔትትሪክ ሠርቷል ።  ኪሊያን እምባፔ በ27 ከመረብ ያረፉ ኳሶች የላሊጋው ኮከብ ግብ አግቢ ነው ። የባርሴሎናው ሮቤርት ሌቫንዶቭስኪ በ25 ግብ ይከተለዋል ። 

 ባርሴሎና በላሊጋው ሪያል ማድሪድን 4 ለ3 በማሸነፍ ለዋንጫ ግስጋሴውን ቀጥሏል
በኮፓ ደ ሬይ ዋንጫውን ያነሳው ባርሴሎና በላሊጋውም ሪያል ማድሪድን 4 ለ3 በማሸነፍ ለዋንጫ ግስጋሴውን ቀጥሏልምስል፦ Borja Suarez/REUTERS

ባርሴሎና በትናንቱ ግጥሚያ 94ኛ ደቂቃ ላይ በሎፔዝ አምስተኛ ግብ ቢያስቆጥርም ኳሷን ቀደም ብሎ በእጁ በመንካቱ ግቡ ተሽሯል ። ብርቱ ፍልሚያ የታየበት የሁለቱ ቡድኖች ግጥሚያ፦ በ97ኛው ደቂቃ ላይ በባርሴሎና የ4 ለ3 ድል ተጠናቅቋል ። ከ2 ለ0 ተነስቶ በማሸነፍ 82 ነጥብ የሰበሰበው ባርሴሎና እና ጀርመናዊው አሰልጣኝ ዲተር ሐንስ ፍሊክ ፈንጥዘዋል ። በ75 ነጥቡ የተወሰነው ሪያል ማድሪድ እና አሰልጣኙ ካርሎ አንቼሎቲም አንገታቸውን ደፍተዋል ።  20 ቡድኖች ያሉት የስፔን ላሊጋ ሊጠናቀቅ ሦስት ዙር ጨዋታዎች ይቀሩታል ። የሚያዝያ 20 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የፊታችን ሐሙስ ማታ ቀጣይ 36ኛ ጨዋታውን ከኢስፓኞል ጋር የሚያደርገው ባርሴሎና ካሸነፈ ዋንጫውን መውሰዱን ያረጋግጣል ። በላሊጋው 14ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ኢስፓኞል ጨዋታውን ቢያሸንፍ በቀጣይ የአውሮጳ ኮንፈረንስ ሊግ ማጣሪያ ተሳታፊ ለመሆን ጭላንጭል ዕድል ይኖረዋል ። ሆኖም በማጣሪያው ተሳታፊ ለመሆን ባርሴሎናን ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ ቀሪ ሦስት ጨዋታዎቹን ማሸነፍ ይጠበቅበታል ። የሐሙሱ ጨዋታ ለኤስፓኞል ብርቱ ፈተና ሲሆን ለባርሴሎና ዋንጫውን መውሰዱን የሚያረጋግጥበት ወሳኝ ግጥሚያ ። 

አርሰናል ከኋላ ተነስቶ በሊቨርፑል ከመሸነፍ ተርፏል

አርሰናል የፕሬሚየር ሊጉን ዋንጫ አስቀድሞ መውሰዱን ያረጋገጠው ሊቨርፑልን አንፊልድ ውስጥ ትናንት ገጥሞ ከ2 ለ0 በመነሳት አቻ ተለያይቷል ። 83  ነጥብ ላለው ሊቨርፑል የትናንቱ ግጥሚያ ምንም የሚፈይደው ነገር ባይኖርም 68 ነጥብ ላለው አርሰናል ግን ወሳኝ ነበር ። በሻምፒዮንስ ሊግ የግማሽ ፍጻሜ ባፓሪ ሳንጃርሞ የተሰናበተው አርሰናል የትናንቱን የፕሬሚየር ሊግ ጨዋታ አሸንፎ ቢሆን ኑሮ የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊነቱን መቶ በመቶ ያረጋግጥ ነበር ። በፕሬሚየር ሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ሰባተኛ ላይ የሚገኘው ኖቲንግሀም ፎረስት እንኳን በ62 ነጥቡ ወደ ሻምፒዮንስ ሊግ የማለፍ ዕድል አለውና ። 

የአርሰናሉ ቡካዮ ሳካ በሻምፒዮንስ ሊግ ከፒኤስጂ ጋር ወሳኝ ግብ ከሳተ በኋላ
የአርሰናሉ ቡካዮ ሳካ በሻምፒዮንስ ሊግ ከፒኤስጂ ጋር ተጫውተው በተሸነፉበት ወሳኝ ግጥሚያ ወቅትምስል፦ Neal Simpson/Imago Images

ለአውሮጳ ሊግ የምድብ ጨዋታ የማለፍ ዕድል ይዞ በስድስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አስቶን ቪላ ነጥቡ 63 ነው ። ቀሪ ሁለት ጨዋታዎቹን ካሸነፈ ነጥቡን ወደ 69 ያደርሳል ። ያም በመሆኑ 68 ነጥብ ያለው አርሰናል የሻምፒዮስ ሊግ ተሳታፊነቱን የሌሎች ቡድኖችን ውጤት ሳይጠብቅ ለማረጋገጥ ከቀጣይ ጨዋታዎቹ ቢያንስ አንዱን ማሸነፍ ይጠበቅበታል ። በርካታ የግብ ክፍያ ስላለውም አንድ ጨዋታ አቻ ቢወጣም ያዋጣዋል ።

ኢፒስዊች ታወን፣ ላይስተር ሲቲ እና ሳወዝሀምፕተን ወደ ሁለተኛው ዲቪዚዮን ወራጆች ናቸው ። በእነሱ ምትክ ባለፈው ሳምንት የሁለተኛ ዲቪዚዮን ዋንጫውን የወሰደው ሊድስ ዩናይትድ ወደ ዋናው ፕሬሚየር ሊግ ማለፉን አረጋግጧል ። ሌላኛው ማለፉን ያረጋገጠ ቡድን በርንሌይ ሲሆን፦ ለቀሪ ሦስተኛ ቦታ ደግሞ ሼፊልድ ዩናይትድ፣ ሰንደርላንድ፣ ኮንቬንትሪ እና ብሪስቶል ሲቲ ይጋጠማሉ ።

ሐምቡርግ ወደ ዋናው ቡንደስሊጋ አለፈ

በጀርመን ቡንደስሊጋ፦ ሆልሽታይን ኪዬል እና ቦሁም ወደ ሁለተኛ ዲቪዚዮን መውረዳቸው የተረጋገጠ ቡድኖች ናቸው ። በእነሱ ምትክ ሐምቡርግ ወደ ዋናው ቡንደስሊጋ ማለፉን አረጋግጧል ። አንድ ጨዋታ እየቀረ ሁለተኛ ሆኖ የሚጨርስ ቡድን ማንነት ገና ዐልታወቀም ። በዋናው ቡንደስሊጋ 29 ነጥብ ሰብስቦ 16ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ሐይደንሀይም ከሁለተኛ ዲቪዚዮን ሦስተኛ ደረጃ ይዞ ካጠናቀቀው ቡድን ጋር በደርሶ መልስ ይጋጠማል ። ከሁለቱ የአሸነፈ ቡድን የቀጣይ ቡንደስሊጋ ተሳታፊ ቦታ መያዙን ያረጋግጣል ። የመጋቢት 29 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

በሁለተኛ ዲቪዚዮን ቡንደስሊጋ ከአንደኛ እስከ አራተኛ ደረጃ ያሉት ቡድኖች የሰበሰቡት ነጥብ በቀጥታ ወደ ቡንደስሊጋው ለማለፍ ዕድል ይሰጣቸዋል ። አንድ ዙር ቀሪ ጨዋታ እየቀረ ሐምቡርግ በ59 ነጥብ ይመራል ።  ኮሎኝ በ58 ይከተላል ። ኤልቨርስበርግ እና ፓዴርቦን 55 ነጥብ አላቸው ።  ዱይስልዶርፍ እና ካይዘርስላውተርንም በ53 ነጥባቸው ገና የማለፍ ዕድላቸው አልመከነም።

አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ
አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ በጀርመን ቡንደስሊጋ ምሥጢር ሁኖ የቆየውን  ከባዬርን ሌቨርኩሰን የመለየቱን ጉዳይ አረጋግጧልምስል፦ Harry Langer/dpa/picture alliance

ዣቪ አሎንሶ ከባዬርን ሌቨርኩሰን መለየቱን ይፋ አድርጓል 

አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ በጀርመን ቡንደስሊጋ ምሥጢር ሁኖ የቆየውን  ከባዬርን ሌቨርኩሰን የመለየቱን ጉዳይ አረጋግጧል ። ባዬርን ሌቨርኩሰንን ከፍተኛ ደረጃ ላይ ያደረሰው ዣቪ አሎንሶን ሪያል ማድሪድ በዘንድሮ የጨዋታ ዘመን መጠናቀቂያ ይጠብቀዋል ። ዣቪ አሎንሶ ባለፈው ሳምንት ዐርብ በነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ የባዬርን ሌቨርኩሰን ውሉ ለመጠናቀቁ ገና አንድ ዓመት ይቀረው እንደነበረም ገልጧል ።

በሌላ ዜና፦ ለባየርን ሙይንሽን የረዥም ዘመን ተጫዋች በመሆን ክብረ ወሰን የሰበረው አጥቂ የ35 ዓመቱ ቶማስ ሙይለር ከቡድኑ ስንብት ተደረገለት ። በአሊያንትስ አሬና ቅዳሜ ዕለት የተሰናበተው በቡንደስሊጋው ቦሩስያ ሞይንሽንግላድባኅን 2 ለ0 ካሸነፉ በኋላ ነው ።  ቶማስ ሙይለር ለባየርን ሙይንሽን  750 ጊዜ ተሰልፎ ተጫውቷል ። የዘንድሮውን ጨምሮ 13 የቡንደስሊጋ ዋንጫዎችን ቡድኑ ሲያሸንፍ አብሮ ነበር ። ለሁለት ጊዜ የሻምፒዮንስ ሊግ እንዲሁም በጀርመን ብሔራዊ ቡድኑ እንደ ጎርጎሪዮስ አቆጣጠር በ2014 የዓለም ዋንጫዎችንም ማንሳት ችሏል ። ቶማስ ሙይለር በባየር ሙይንሽን ታሪክ ከጌርድ ሙይለር (570) እና ሮቤርት ሌቫንዶብስኪ  (344) ቀጥሎ 248 ግቦችንን በማስቆጠር ሦስተኛ ግብ አግቢ ነው ።  222 ግብ ሊሆኑ የሚችሌ ኳሶችንም በማመቻቸት ይታወቃል። 

ማንተጋፍቶት ስለሺ

እሸቴ በቀለ

 

ማንተጋፍቶት ስለሺ ሥዩም Mantegaftot Sileshi ዜና አዘጋጅ፤ መርኃ ግብር መሪ፤ የሳምንታዊ ስፖርት አዘጋጅ ነው፥ በአጭር ፊልም የበርካታ ዓለም አቀፍ ተሸላሚው ማንተጋፍቶት የቪዲዮ ዘገባዎችንም ያዘጋጃል።@manti