1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የየካቲት 17 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ የካቲት 17 2017

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተለያዩ የማራቶን ውድድሮች በወንድም በሴትም ፉክክር ድል ተቀዳጅተዋል። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ሊቨርፑል በግስጋሴው ቀጥሎ በ11 ነጥብ ልዩነት ተከታዩ አርሰናልን ርቋል ። በመጀመሪያው ግጥሚያ በውድድሩ ማብቂያ ላይ በዩጋንዳ አቻቸው የተሸነፉት ሉሲዎቹ በመልሱ ግጥሚያ ረቡዕ ይፋለማሉ ።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4qyeB
Fußball Bundesliga | FC Bayern München - Eintracht Frankfurt
ምስል፦ Frank Hoermann/Sven Simon/IMAGO

የየካቲት 17 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተለያዩ የማራቶን ውድድሮች በወንድም በሴትም ፉክክር ድል ተቀዳጅተዋል ።  በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ሊቨርፑል በግስጋሴው ቀጥሎ በ11 ነጥብ ልዩነት ተከታዩ አርሰናልን ርቋል ። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው አርሰናል በገዛ ሜዳው በዌስትሐም መሸነፉ በዋንጫ ተፎካካሪነቱ ላይ ጋሬጣ ደቅኗል ። ቀጣይ ጨዋታው ሦስተኛ ደረጃ ላይ በሚገኘው ኖቲግንሀም ፎረስት ሜዳ ነው ። በጀርመን ቡንደስሊጋ መሪው ባዬርን ሙይንሽ እና ተከታዩ ባዬር ሌቨርኩሰን ተጋጣሚዎቻቸውን አሸንፈዋል ። ላይፕትሲሽ ከታችኛው ዲቪዚዮን ባደገው እና ወራጅ ቀጣናው ግርጌ ላይ በሚገኘው ሐይደንሀይም ተፈትኖ አቻ ወጥቷል ።  በመጀመሪያው ግጥሚያ በውድድሩ ማብቂያ ላይ  በዩጋንዳ አቻቸው የተሸነፉት ሉሲዎቹ  በመልሱ ግጥሚያ ረቡዕ ይፋለማሉ ።

አትሌቲክስ

በጃፓን ኦሳካ፣ ደቡብ ኮሪያ ዴጉ እና በስፔን የሴቪያ ማራቶን ሩጫ ፉክክሮች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ድል ተቀዳጅተዋል ። በተለይ በጃፓን ኦሳካ የማራቶን ሩጫ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሁለቱም ፆታ በበላይነት አጠናቅቀዋል ።

በሴቶች የማራቶን ፉክክር ኢትዮጵያውያቱ ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ተከታትለው በመግባት ብቃታቸውን አስመስክረዋል ። አትሌት ዋጋነሽ መካሻ (2:26:33) በመሮጥ አንደኛ ወጥታለች ። አትሌት አፈራ ጎድፋይ እና ኩባ ዓለሙ በዋጋነሽ በ7 እና 10 ሰከንዶች ተቀድመው ሁለተኛ እና ሦስተኛ ደረጃ አግኝተዋል ።

በወንዶች ተመሳሳይ ሩጫ ደግሞ ኢትዮጵያዊው አትሌት ይሁንልኝ አዳነ የራሱ ምርጥ ሰዓትን በ(2:05:37)በማስመዝገብ የቦታውን ሰዓት ጭምር አሻሽሎ ነው በአንደኝነት ያጠናቀቀው ። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት አብዲሳ ቶላ የጃፓኑ ሯጭ ርዮታ ኮንዶን በ13 ሰከንዶች ተከትሎ ሦስተኛ ደረጃ (2:05:52)አግኝቷል ። አትሌት ጌትነት ሞላም ሌላኛው ጃፓናዊ ክዮሃይ ሆሶያን ተከትሎ በአምስተኛነት አጠናቅቋል ።  የየካቲት 10 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ትናንት በተከናወነው የኮርያ -ዴጉ ዓለምአቀፍ የማራቶን ሩጫ ፉክክርም ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች አሸንፈዋል ። በሴቶች ውድድር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት መሠረት በለጠ (2:24:08) በመሮጥ አንደኛነት አጠናቃለች ። ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት አትሌት ትእግስት ግርማ ከባህሬኗ ሯጭ ሩት ጄቤት ለጥቂት በ2 ሰከንዶች ተበልጣ ሦስተኛ ደረጃ አግኝታለች ። ሩት ጄቤት ውድድሯን ያጠናቀቀችው (2:25:43) በመሮጥ ነው ።

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተለያዩ የማራቶን ውድድሮች በወንድም በሴትም ፉክክር ድል ተቀዳጅተዋል  
ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተለያዩ የማራቶን ውድድሮች በወንድም በሴትም ፉክክር ድል ተቀዳጅተዋል  ምስል፦ Florian Gaul/greatif/picture alliance

በወንዶች ተመሳሳይ የሩጫ ፉክክር ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች አዲሱ ጎበና (2:05:22)እና ደጀኔ መገርሣ (2:05:59)ሁለተኛ እና ሦስተኛ ደረጃ አግኝተዋል ። በዚህ ፉክክር፦ ታንዛኒያዊው ጋብርኤል ጌአይ (2:05:20)በመሮጥ አንደኛ ወጥቷል ።

በስፔን የሴቪያ ማራቶንም ኢትዮጵያውያን ድል ተቀዳጅተዋል ።  አትሌት ሰለሞን ባረጋ በመጀመሪያ ጊዜ የማራቶን ውድድሩ (2:05:15) በመሮጥ አሸንፏል ። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አዲሱ አትሌት ተስፋሁን ( 2:06:27) ሮጦ ሁለተኛ ደረጃ አግኝቷል ። 

በሴቶቹ ተመሳሳይ ርቀት ፉክክር፦ ኢትዮጵያዊቷ አትሌት አንቺንአሉ ደሴ (2:22:17) በመሮጥ አሸንፋለች ። የፈረንሣይዋ አትሌት ማኖን ትራፕ እና ኬንያዊቷ ሲንቲያ ኮስገይ ሁለተኛ እና ሦስተኛ ሁነዋል።  ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት ትእግስት ገዛኸኝ ሞሮኮያዊቷ ኮታር ቦውላይድን ተከትላ በአምስተኛ ደረጃ (2:24:25) አጠናቃለች ።

እግር ኳስ

ኢትዮጵያ የሴቶች ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን (ሉሲዎቹ) ከዩጋንዳ አቻው ጋር ካምፓላ ውስጥ ባደረገው የመጀመሪያ ግጥሚያ በዩጋንዳ ቡድን የ2 ለ0 ሽንፈት ገጥሞታል ። መደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜው ሊጠናቀቅ አንድ ደቂቃ እስኪቀረው ድረስ በሁለቱም በኩል አንድም ግብ አልተቆጠረም ነበር ። ሁለቱ ግቦች የተቆጠሩት በ89 እና 93ኛው ደቂቃዎች ላይ ነበር ። ለዩጋንዳ ቡድን 89ኛው ደቂቃ ላይ ይና ናሙሌሜ፤ እንዲሁም መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አብቅቶ በጭማሪው 3ኛ ደዲቃ ላይ ፋዚላ ኢክዋፑት ሁለተኛውን አስቆጥረዋል ። አዲስ አበባ ውስጥ ረቡዕ የመልስ ጨዋታ ይኖራል ።

የአዲስ አበባ ስታዲየም መቼ ይሆን እድሳቱ ተጠናቆ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን ማስተናገድ የሚጀምረው?
የአዲስ አበባ ስታዲየም መቼ ይሆን እድሳቱ ተጠናቆ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን ማስተናገድ የሚጀምረው?ምስል፦ Omna Tadel

ፕሬሚየር ሊግ

ትናንት ወደ ኤታድ ስታዲየም ያቀናው ሊቨርፑል ማንቸስተር ሲቲን በገዛ ሜዳው ጉድ አድርጎታል ። ማንቸስተር ሲቲ ምንም እንኳን በገዛ ሜዳው ሽንፈት ቢገጥመውም በኳስ ይዞታ ግን ከሊቨርፑል በልጦ ታይቷል ። በተለይ ጄሬሚ ዶኩ በክንፍ በኩል በኳስ ጥበቡ እና በፍጥነቱ ተከላካዮችን ሲያስጨንቅ አምሽቷል ። ሊቨርፑሎች ሁለት ግቦችን ካስቆጠሩ በኋላ እጅግ ወደ ኋላ ተመልሰው በብርቱ መከላከላቸው እና በመልሶ ማጥቃት ላይ ማተኮራቸው ማንቸስተር ሲቲን እንደጎዳው ገልጧል ።  ጄሬሚ ዶኩ በተለይ የሊቨርፑል ተከላካይ አሌክሳንደር አርኖልድን በኳስ ጥበብ፤ በተክለ ሰውነት እና ድንገት አፈትልኮ በማለፍ ሲያንገላታው አምሽቷል ። የየካቲት 3 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ለሊቨርፑል ሞሐመድ ሣላኅ እና ዶሚኒክ ሶቦስላይ በ14ኛው እና 37ኛው ደቂቃ ላይ ከመረብ አሳርፈዋል ። ሞሐመድ ሣላኅ የትናንቱን ጨምሮ እስካሁን 25 ኳሶችን ከመረብ በማሳረፍ በኮከብ ግብ አግቢነት ይመራል ። የኒውካስል አጥቂ አሌክሳንደር ይሳቅ ሞሐመድ ሣላኅን በመከተል እንደ ማንቸስተር ሲቲው ኧርሊንግ ኦላንድ 19 ኳሶችን አስቆጥሮ ሁለተኛ ኮከብ ግብ አግቢ ነው ። ሊቨርፑል አሌክሳንደርን ለማስመጣት ፍላጎት ቢኖረውም ኒውካስትል በጠየቀው የ190 ሚሊዮን ዶላር ግድም የመልቀቂያ ክፍያ ግን እንደማይስማማ ተገልጧል ። ሊቨርፑል ይህን ያህል እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ አንድ ተጨዋች ላይ ብቻ ማፍሰስ እንደማይፈልግም ተጠቅሷል ። 

የሊቨርፑል አሰልኝ አርኔ ስሎ
የሊቨርፑል አሰልኝ አርኔ ስሎምስል፦ Propaganda Photo/Imago Images

በፕሬሚየር ሊጉ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው ሊቨርፑልን በ11 ነጥብ የሚከተለው አርሰናል  ቅዳሜ ዕለት በገዛ ሜዳው በዌስትሐም 1 ለ0 መሸነፉ በዋንጫ ተፎካካሪነቱ ላይ ጋሬጣ ደቅኖበታል ። ቀጣይ ጨዋታው ሦስተኛ ደረጃ ላይ በሚገኘው ኖቲግንሀም ፎረስት ሜዳ ነው ። ትናንት በኒውካስል የ4 ለ3 ሽንፈት ያስተናገደው ኖቲግንሀም ፎረስት 43 ነጥብ አለው ። አርሰናል 53 ነጥቦችን ሰብስቧል ።  ቅዳሜ ዕለት በአስቶን ቪላ 2 ለ1 የተሸነፈው ቸልሲ ነገ ማታ ከሳውዝሐምፕተን ጋር ይጋጠማል ። ዎልቭስ ከፉልሀም፣ ክሪስታል ፓላስ ከአስቶን ቪላ እንዲሁም ብራይተን ከቦርመስ ጋርም ነገ ይጫወታሉ ። የጥር 26 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ቡንደስ ሊጋ

የጀርመን ቡንደስ ሊጋን በ58 ነጥብ የሚመራው ባዬርን ሙይንሽን ትናንት አይንትራኅት ፍራንክፉርትን 4 ለ0 ድባቅ መትቷል ። በ50 ነጥብ የሚከተለው ባዬር ሌቨርኩሰን በበኩሉ ቅዳሜ ዕለት ሆልሽታይን ኪዬልን 2 ለ0 አሸንፏል ። አይንትራኅት ፍራንክፉርት በ42 ሦስተኛ፣ ቬርደር ብሬመንን 5 ለ0 ያንኮታኮተው ፍራይቡርግ በ39 ነጥብ አራተኛ፣ ሳንክት ፓውሊን 2 ለ0 ያሸነፈው ማይንትስ በ38 አምስተኛ ሆነው ይከታተላሉ ። ከታችኛው ዲቪዚዮን ካደገው ሐይደንሀይም ጋር ትናንት ሁለት እኩል የተለያየው ላይፕትሲሽ ከማይንትስ በግብ ክፍያ ተበልጦ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። ሐይደንሀይም ቦሁም እና ሆልሽታይን ኪዬል ከ16ኛ እስከ 18ኛ ወራጅ ቀጣና ውስጥ ይገኛሉ ።

የ28 ዓመቱ ጊኒያዊ አጥቂ ሴሮህ ጊራሲ
የ28 ዓመቱ ጊኒያዊ አጥቂ ሴሮህ ጊራሲ በ91 የቡንደስሊጋ ጨዋታዎች 56 ኳሶችን ከመረብ ማሳረፍ ችሏልምስል፦ Marcus Hirnschal/osnapix/IMAGO

የተለያዩ የሩብ ፍጻሜ ግጥሚያዎች

ነገ እና ከነገ በስትያ የተለያዩ የሩብ ፍጻሜ ግጥሚያዎች ይኖራሉ ። በስፔን ዓመታዊ የጥሎ ማለፍ ዋንጫ ውድድር (copa del rey)፦ ነገ ባርሴሎና አትሌቲኮ ማድሪድን ያስተናግዳል ። ከነገ በስትያ ደግሞ ሪያል ማድሪድ ከሪያል ሶሴዳድ ሳን ሠባስቲያን ጋር ይጫወታል ። የመልስ ጨዋታዎች ሳምንት ይኖራሉ ። 

በጣሊያን ዋንጫ (Coppa Italia)የሩብ ፍጻሜ ግጥሚያ፦ ኢንተር ሚላን ነገ ማታ ላትሲዮ ሮምን ያስተናግዳል ። በበነጋታው ደግሞ፦ ጁቬንቱስ ከኢምፖሊ ጋር ይጋጠማል ።  ቀደም ባሉ ጨዋታዎች ቦሎኛ አታላንታን 1 ለ0፤ ኤሲ ሚላን ኤኤስ ሮምን 3 ለ1 አሸንፈው ወደ ግማሽ ፍጻሜው ማለፋቸውን አረጋግጠዋል ። በአውሮጳ የኔሽን ሊግ እግር ኳስ የምድብ አንድ መሪ ኦስትሪያ እና ተከታዩ ጀርመን ነገ ማታ ይጋጠማሉ ። ምድቡን የኦስትሪያ ቡድን በ3 ነጥብ ይመራል፣ ጀርመን እና ኔዘርላንድ በ1 ነጥብ ይከተላሉ ። የስኮትላንድ ቡድን ያለምንም ነጥብ 4ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። የጥር 19 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

በጀርመን ፖካል (DFB)ዋንጫ ለግማሽ ፍጻሜ፦ ነገ ማታ አርሜኒያ ቢሌፌልድ ቬርደር ብሬመንን ይገጥማል ። በበነጋታው ረቡዕ ደግሞ በቡንደስሊጋው ተደጋጋሚ ሽንፈት የገጠመው ላይፕትሲሽ ከቮልፍስቡርግ ጋር ይጫወታል ። ቀደም ሲል በነበሩ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች፦ ሽቱትጋርት አውግስቡርግን 1 ለ0 እንዲሁም ባዬር ሌቨርኩሰን ኮሎኝን 3 ለ2 አሸንፈዋል ።

የጀርመን እግር ኳስ ማኅበር አዲስ ለሚመሠረተው መንግሥት ጥሪ

ቬኑስ ዊሊያምስ
ቬኑስ ዊሊያምስ ምስል፦ AP

የጀርመን እግር ኳስ ማኅበር (DFB) አዲስ ለሚመሠረተው የጀርመን መንግሥት ባለ ዐሥር ነጥብ ጥያቄዎችን አቅርቧል ። ከጥያቄዎቹ መካከል፦ በፌዴራል መራኄ መንግሥት ስር የስፖርት ሚንስትር ዴኤታ ይኑር፣ ለትርፍ ላልተመሠረቱ ቡድኖች የቀረጥ እፎይታ ይደረግ እና በስፖርቱ የከባቢ አየር ጥበቃ የበለጠ ትኩረት ይሰጠው የሚሉት ነጥቦች ይገኙበታል ። ግዙፉ ማኅበር 24,000 ቡድኖች እና ወደ 8 ሚሊዮን ግድም አባላትን ያቀፈ ነው ።

የሜዳ ቴኒስ

የ44 ዓመቷ የሜዳ ቴኒስ የዓለማችን ድንቅ ተጨዋች ቬኑስ ዊሊያምስ የፊታችን እሁድ ሕንድ ውስጥ በሚከፈተው የኢንዲያን ዌልስ ውድድር ተካፋይ እንደማትሆን ዐሳወቀች ። አሜሪካዊቷ የሜዳ ቴኒስ ተጨዋች በውድድሩ እንደምትሳተፍ አዘጋጆቹ በድረ ገጻቸው ይፋ አድርገው ነበር ። ሆኖም ቬኑስ ስለውድድሩ አስቀድሞ ስላልተነገረኝ እና ሌላ ጉዳይ ስላለኝ በእሁዱ ግጥሚያ አልሳተፍም ብላለች ።  ቬኑስ በእሁድ ውድድር ለ10ኛ ጊዜ እንድትሳተፍ አዘጋጆቹ ሁኔታዎችን አመቻችተውላት እንደነበር ተዘግቧል ። ሚያሚ ውስጥ ከአንድ ዓመት በፊት ከተደረገው ውድድር ወዲህ ሴሬና ተወዳድራ ዐታውቅም ።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር   

 

ማንተጋፍቶት ስለሺ ሥዩም Mantegaftot Sileshi ዜና አዘጋጅ፤ መርኃ ግብር መሪ፤ የሳምንታዊ ስፖርት አዘጋጅ ነው፥ በአጭር ፊልም የበርካታ ዓለም አቀፍ ተሸላሚው ማንተጋፍቶት የቪዲዮ ዘገባዎችንም ያዘጋጃል።@manti