1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የክርስቲያን ዴሞክራት የክርስቲያን ሶሻል ኅብረት እና የሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ ስምምነት

ረቡዕ፣ መጋቢት 3 2017

ሁለቱ ፓርቲዎች ተጣምረው መንግስት ለመመስረት ከበቁ እንደሚሰናበተው መንግስት ሁሉ ለዩክሬን የሚሰጡትን እርዳታ የመቀጠልና እቅድ አላቸው።ዶናልድ ትራምፕ ከአትላንቲክ ወዲያ ማዶ ያለውን ግንኙነት ካናጉ በኋላ የሰሜን አትላንቲክ የጋራ መከላከያ ቃል ኪዳን ድርጅት ወደፊት ተጠናክሮ መቀጠሉ ያጠራጠራቸው ሜርዝ የጀርመንን ጦር ኃይል ለማጠናከርም ይፈልጋሉ።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4reln
Deutschland Berlin 2025 | Pressekonferenz mit Spitzen von CDU, CSU und SPD
ምስል፦ Markus Schreiber/AP/picture alliance

የክርስቲያን ዴሞክራትና የክርስቲያን ሶሻል ኅብረት እንዲሁም የሶሻል ዴሞክራቶች ፓርቲ የመጀመሪያ ደረጃ ስምምነት

ባለፈው ሳምንት መጨረሻ የመጀመሪያ ደረጃ ስምምነት ላይ የደረሱት የጀርመን ምርጫ አሸናፊ እህትማማቾቹ የክርስቲያን ዴሞክራትና የክርስቲያን ሶሻል ኅብረት ፓርቲዎች በምርጫው ሦስተኛ ደረጃ ካገኘው ከሶሻል ዴሞክራቶቹ ፓርቲ SPD ጋር ጥምር መንግስት ለመመስረት ትልቅ እርምጃ ላይ ደርሰናል ሲሉ አስታውቀዋል። የአሸናፊዎቹ እህትማማች ፓርቲዎች እጩ መራኄ መንግስት ፍሪድሪሽ ሜርስ ንግግሩ ባለቀበት ባለፈው ቅዳሜ እንዳሉት ሁለቱ ወገኖች በሦስት ዋና ዋና ፖሊሲዎች ላይ ተስማምተዋል።

እነርሱም የምርጫው ዋና ትኩረት የነበሩት ፍልሰት ፣ ፋይናንስ የስራ ገበያና ኤኮኖሚ ናቸው። የበርሊኑ የመጀመሪያ ደረጃው ንግግር ሲያበቃ ሜርስ እንደተናገሩት ሁለቱ ወገኖች ሰነድ የሌላቸውን ስደተኞችና ተገን ጠያቂዎች ከጀርመን ድንበሮች ለመመለስ አቅደዋል።«ከአውሮጳ ሀገራት ጎረቤቶቻችን ጋር በመተባበር  በጋራ ድንበሮቻችን ላይ የተገን ጥያቄ ማመልከቻዎችን እንቀበልም። ሕገወጥ ስደትን ለመቀነስ ማናቸውንም ሕገ መንግስታዊ እርምጃዎች ለመውሰድ እንፈልጋለን። ጥምሩ መንግስት ከሚመሰረትበት የመጀመሪያ ቀን አንስቶ የድንበር ቁጥጥርን በከፍተኛ ደረጃ እናጠናክራለን። የድንበር ቁጥጥሩንም የተገን ጥያቄን በከፍተኛ ደረጃ ለመቀነስ እንጠቀምበታለን።»በጀርመን ምርጫ አሸናፊው ፓርቲ የሚመሰርተው መንግስት ከፊቱ ምን ይጠብቀዋል ?

ከዚህ ሌላ ፓርቲዎቹ በቅርቡ የተሻሻለው የጀርመን የዜግነት ሕግ እንዲቀጥልም ተስማምተዋል። በፍልስት ጉዳይ ላይ የተለያየ አቋም የነበራቸው ሁለቱ ፓርቲዎች በመጀመሪያ ደረጃ ንግግራቸው ለተስማሙባቸው ስለነዚህ ጉዳዮች የጠየቅናቸው ለበርካታ ዓመታት ጀርመን የኖሩት ትውልደ ኢትዮጵያዊው የምጣኔ ኃብትና አስተዳደር ባለሙያው ዶክተር ጸጋዬ ደግነህ ዓላማቸውን ምን እንደሆነ ተናግረዋል። ቀጣዩ የጀርመን መራኄ መንግስት እንደሚሆኑ የሚጠበቀው ሜርስ በርካታ ፈተናዎች የተጋረጡበትን የጀርመንን ኤኮኖሚ የማነቃቃት እቅድ አላቸው። ከዚሁ ጋር ቀረጥ በመቀነስ በተለይ መካከለኛ ገቢ ያለውን የኅብረተሰብ ክፍል የኑሮ ጫና ለማቅለል የዋጋ ቅነሳዎችን ለማድረግም አቅደዋል። እነዚህና ሌሎችም አሁን በሚሰናበተው መንግስት ተግባራዊ ያልሆኑ ማበረታቻዎችም በስምምነቱ ውስጥ ተካተዋል እንደ ዶክተር ጸጋዬ።

ፍሪድሪሽ ሜርስና ላርስ ክሊንግቤል
ፍሪድሪሽ ሜርስና ላርስ ክሊንግቤልምስል፦ RALF HIRSCHBERGER/AFP via Getty Images

የሶሻል ዴሞክራቶቹ ፓርቲ ተባባሪ መሪ እና በጀርመን ፓርላማ የፓርቲው አባላት ቡድን መሪ ላርስ ክሊንግቤል እንደሚሉት የሠራተኞች ዝቅተኛ ክፍያ በሰዓት 15 ዩሮ ወይም 16 ዶላር እንዲሆን ስምምነት ላይ ደርሰዋል። ጥምር መንግስት ለመመስረት ወደ ድርድር የሚሸጋገሩት ሁለቱ ፓርቲዎች ተጣምረው መንግስት ለመመስረት ከበቁ እንደሚሰናበተው መንግስት ሁሉ ለዩክሬን የሚሰጡትን እርዳታ የመቀጠልና እቅድ አላቸው። ከዚሁ ጋር በተለይ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከአትላንቲክ ወዲያ ማዶ ያለውን ግንኙነት ካናጉ በኋላ ፣የሰሜን አትላንቲክ የጋራ መከላከያ ቃል ኪዳን ድርጅት ወደፊት ተጠናክሮ መቀጠሉ ያጠራጠራቸው ሜርዝ የጀርመንን ጦር ኃይል ለማጠናከርም ይፈልጋሉ።የጀርመን ምርጫ 2025 ፋይዳ ተግዳሮቶቹና አስተምህሮቱ

በጎረቤቶቻቸው በሜክሲኮና በካናዳ ላይ የታሪፍ ጭማሪ ዛቻቸውን የቀጠሉት ትራምፕ ከዚያ ቀጥሎ ቀደም ሲል ሲዝቱ እንደከረሙት ትኩረታቸውን ከአውሮጳ ኅብረት አባል ሀገራት በሚገቡ ምርቶች ላይ እንደሚያደርጉ ይጠበቃል። ትራምፕ እንዳሉትም በታሪፍ ጭማሪው አቋማቸው ከጸኑ ጀርመን ብዙ ተግዳሮቶች ሊገጥሟት ይችላል ተብሎ እንደሚጠበቅ የምጣኔ ሀብት ባለሞያው ዶክርት ጸጋዬ ያስረዳሉ። ይህን ተከትሎም ጀርመንን ጨምሮ የኅብረቱ አባል ሀገራት የአጸፋ እርምጃዎችን መውሰዳቸው እንደማይቀር ይገመታል።

የክርስቲያን ሶሻል ኅብረት መሪ ማርኩስ ዞደር ፣ የክርስቲያን ዴሞክራት ኅብረት መሪ ፍሪድሪሽ ሜርስ ፣ የSPD የፓርላማ አባላት መሪ ፤ ሳስክያ ኤስከን የSPD ሊቀ መንበር
የክርስቲያን ሶሻል ኅብረት መሪ ማርኩስ ዞደር ፣ የክርስቲያን ዴሞክራት ኅብረት መሪ ፍሪድሪሽ ሜርስ ፣ የSPD የፓርላማ አባላት መሪ ፤ ሳስክያ ኤስከን የSPD ሊቀ መንበር ምስል፦ Kay Nietfeld/dpa/picture alliance

ወደፊቱ የሚመሰረተው የጀርመን ጥምር መንግሥት ለዩክሬን የሚሰጠው እርዳታ  እንዲቀጥልና የመከላከያ ወጪን ለመጨመር እንዲሁም ለመሰረተ ልማት ግንባታ አስፈላጊ ለሆኑ ወጪዎች ገንዘብ ለማግኘት ጥብቅ የሆነውን የጀርመንን ሕገ መንግስታዊ የእዳ ህጎች ለማላላትም ስምምነት ላይ ደርሰዋል። ይህን ማሻሻያ በፓርላማው ለማሳለፍ ሁለት ሦስተኛ ድምጽ ስለሚያስፈልግ ደግሞ በንግግሩ ላይ ያልተሳተፉት የአረንጓዴዎቹ ፓርቲ ድጋፍ ያሻቸዋል። ይህን ድጋፍ ለማግኘት ደግሞ ተጣምረው መንግስት ለመመስረት በዝግጅት ላይ ያሉት ፓርቲዎች ብዙ የማግባባት ስራ ይጠብቃቸዋል።የአሸናፊዎቹ ፓርቲዎች እጩ መራኄ መንግስት ሜርስ ለመንግስት ምስረታ የሚያካሂዱትን ድርድር እስከ መጪው ፋሲካ የመጨረስ ግብ አላቸው።

ኂሩት መለሰ

እሸቴ በቀለ