የእሥራኤል ኢራን ግጭት፤የዩናትድ ስቴትስ እና የአውሮጳ ኅብረት
ረቡዕ፣ ሰኔ 11 2017የእስራኤል መከላከያ ማለዳ ከ50 በላይ ተዋጊ ጀቶችን አሰማርቶ ቴህራን ላይ ጥቃት ማድረሱን አረጋግጧል። በጥቃቱም የኢራንን የኒኩሊየር ማብላያ ማምረቻ ተቋሟትን ማውደሙን አመልክቷል። እንዲያም ሆኖ የት ቦታ ላይ የሚለውን አላብራራም። ኢራን አነስተኛ ሚሳኤሎችን እስራኤል ላይ የመተኮሷን ተከትሎ የእስራኤል የጦር ጀቶች ሌሊቱን ዋና ከተማ ቴህራንን መደብደባቸው ነው የተገለጸው። የእስራኤል ጦር ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጀነራል አይፊ ደፍሪን ሁኔታውን አስመልክተው በሰጡት መግለጫ ለሦስት ሰዓት የዘለቀውን ጥቃት እንዲህ ዘርዝረዋል።
«ትናንት ምሽት የአየር ኃይል ተዋጊ ጀቶች፤ በትክክለኛ የስለላ መመሪያ እየታገዙ ቴህራን ላይ ሌላ ጠንካራ ጥቃት ፈጽመዋል። በዚህ መጠነ ሰፊ ጥቃት ከ50 በላይ ተዋጊ ጀቶች ተሳትፈዋል።ሦስት ሰዓታት የወሰደው ጥቃት፤ ሦስት የጥቃት ማዕበል ያካተተ ነበር። በዘመቻው አገዛዙ እንዲቀጥልና ዩራኒየም የማብላላት ተግባሩንን እንዲያጠናክር እንዲያግዙ የታሰቡ የማምረቻ ስፍራዎችን አጥቅተናል። ይህም የኒኩሊየር መርሃግቡሩን ክፍሎች ለማበላሸት ቀደም ሲል ያካሄድናቸው ዘመቻዎች አካል ነው።»
አክለውም ዛሬ ማለዳም የእስራኤል የአየር ኃይል ጀት የኢራንን አምስት የጦር ሄሊኮፕተሮች ለይቶ ማጥቃቱን ተናግረዋል። ቃል አቀባዩ እንደተናገሩት ሄሊኮፕተሮቹ የእስራኤልን አውሮፕላኖች ለማጥቃት ያለሙ ነበሩ። የኢራን ባለሥልጣናት በበኩቸው በሁለቱ ሃገራት ግጭት ውስጥ አሜሪካ ጣልቃ ሳትገባ እንዳልቀረች እየተናገሩ ነው። በሺህዎች የሚቆጠሩ የአሜሪካ ወታደሮች የኢራን የጦር መሳሪያ በሚደርስባቸው ርቀት በሚገኙ ሃገራት ውስጥ መገኘታቸውን በመግለጽም የአጸፋ ጥቃቱ ለአሜሪካም እንደሚተርፍ እየዛቱ ነው።
በካናዳ አስተናጋጅነት የተካሄደው የቡድን ሰባት አባል ሀገራት የመሪዎች ጉባኤ መሪዎቹ ሲጠናቀቅ እሥራኤልና ኢራን ግጭቱን እንዲያበርዱ ጠይቀዋል።ትናንት ብራሰልስ አስቸኳይ ስብሰባ ያካሄዱት የአውሮጳ ኅብረት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮችም ተመሳሳይ ጥሪ አቅርበዋል ። የቡድን ሰባት አባል ሀገራት መሪዎች ና የአውሮጳ ኅብረት ለእስራኤልና ለኢራን ያስተላለፉት ጥሪ ፋይዳና በግጭቱ የአሜሪካን ሚና ላይ የብራሰልሱን ዘጋቢያችንን ገበያው ንጉሴን በስልክ አነጋግረነዋል።
ገበያው ንጉሴ
ኂሩት መለሰ
ታምራት ዲንሳ