1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የኤሉክትሪክ ዋጋ የሚጨምረዉ ለትርፍ አይደለም፣ ሕዳሴ ግድብም ተጠናቅቋል-ባለሥልጣን

ሰለሞን ሙጬ
ሐሙስ፣ ነሐሴ 1 2017

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በቅርቡ ይፋ ያደረገው የኃይል መሸጫ ዋጋ ተቋሙ የኃይል ማመንጫዎችን፣ ማስተላለፊያ እና ማከፋፈያ ጣቢያዎችን ለመገንባት፣ ጥገናዎችን ለማከናወን የሚያወጣውን ወጪ ለመሸፈን የሚያስችል አለመሆኑን ዛሬ ሐሙስ ገልጿል

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4yens
የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ባለሥልጣናት ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ።የኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አሥፈፃሚ እንዳሉት የኤሌክትሪክ ኃይል ዋጋ ጭማሪ የሚደረግበት ለትርፍ አይደለም
የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ባለሥልጣናት ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ።የኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አሥፈፃሚ እንዳሉት የኤሌክትሪክ ኃይል ዋጋ ጭማሪ የሚደረግበት ለትርፍ አይደለምምስል፦ Solomon Muche/DW

የኤሌክትሪክ ዋጋ የሚጨምረዉ ለትርፍ አይደለም፣ ሕዳሴ ግድብም ተጠናቅቋል-ባለሥልጣን

 

ኢትዮጵያ ውስጥ ለአራትዓመታት በየሦስት ወሩ እየጨመረ የሚሄደው የኤሌክትሪክ ኃይል የመሸጫ ዋጋ ማሻሻያ "ትርፍን ታሳቢ ያደረገ አይደለም" ሲል የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታወቀ።የኤሌክትሪክ ሽያጭ ተመን "አሁንም ከዋጋው በታች ነው" ያለው ተቋሙ፤ "ዝቅተኛ ገቢ ያለውን ሕዝብ በማይጎዳ መልኩ" የተሻሻለ ነው ሲል ዛሬ በሰጠው መግለጫ ገልጿል።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አሥፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ የሕዳሴ ግድብ ካለምንም የውጭ ብድር በመንግሥት እና ሕዝብ ተሰርቶ ሙሉ በሙሉ መጠናቀቁን ተናግረዋል።

ኃላፊው አክለው ግድቡ የሚመረቅበት ጊዜ ይፋ ከሆነ ወዲህ በግብጽ በኩል በምርቃቱ ላይ እክል ለመፍጠር "ከፍተኛ ሩጫ አለ" ሆኖም "ውጤቱን ሊቀይሩት አይችሉም" ብለዋል።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በቅርቡ ይፋ ያደረገው የኃይል መሸጫ ዋጋ ተቋሙ የኃይል ማመንጫዎችን፣ ማስተላለፊያ እና ማከፋፈያ ጣቢያዎችን ለመገንባት፣ ጥገናዎችን ለማከናወን የሚያወጣውን ወጪ ለመሸፈን የሚያስችል አለመሆኑን ዛሬ ሐሙስ ገልጿል። እንደ ማሳያም ተቋሙ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተበድሮት የነበረው የ260 ቢሊዮን ብር ዕዳ በመንግሥት መዞሩን ጠቅሷል። የተቋሙ ዋና ሥራ አሥፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ እንዳሉት "የኤሌክትሪክ ኃይል ለሕዝብ ይቀርብ የነበረው በኪሳራ ነበር"

"የምናቀርበው የኤሌክትሪክ ኃይል አሁንም ከዋጋው በታች መሆኑን ነው የሚያሳየው። አሁን ያደረግነው ጭማሪ ምንም ትርፍ ሳይታሰብበት ዋጋን ብቻ እንዲመልስ ታሳቢ በማድረግ ነው የተሠራው።"

የሕዳሴ ግድብን ጨምሮ 20 የኃይል ማመንጫ ጣቢያዎችን የሚያስተዳድረው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አጠቃላይ የማምረት አቅሙ 7 ሺህ 910 ሜጋ ዋት መሆኑን ገልጿል። በዚህ ምክንያት 46 በመቶው የኢትዮጵያ ሕዝብ ኤሌክትሪክ የማያገኝ ከመሆኑም በላይ መቆራረጡ አሁንም ከኤሌክትሪክ አገልግሎት ጋር ያለ የጋራ ችግር ነው ብለዋል ኃላፊው።

"ችግር አለ እውነት ነው። ይህንን ለመቅረፍ በጋራ እየሠራን ነው።"

43 የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ ማማዎች በስርቆት ምክንያት መውደቃቸው፣ በፀጥታ ችግር ምክንያት ተንቀሳቅሶ መገንባት፣ መጠገን አለመቻል ለኃይል መቆራረጥ ምክንያት መሆናቸውም በዚሁ ወቅት ተጠቅሷል። የሕዳሴ ግድብ ላይ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ደጋግመው ስለሰጡት ለግድቡ የገንዘብ ድጋፍ አድርገናል የሚል አስተያየትም ጥያቄ ቀርቦላቸው ምላሽ ሰጥተዋል።

የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ።ዋና ሥራ አስፈፃሚዉ እንዳሉት መስሪያ ቤታቸዉ የኤሌክትሪክ ኃይል ዋጋ የሚጨምረዉ ለትርፍ አይደለም።የሕዳሴ ግድብም ተጠናቅቋል
የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ።ዋና ሥራ አስፈፃሚዉ እንዳሉት መስሪያ ቤታቸዉ የኤሌክትሪክ ኃይል ዋጋ የሚጨምረዉ ለትርፍ አይደለም።የሕዳሴ ግድብም ተጠናቅቋልምስል፦ Solomon Muche/DW

"በዋናነት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከፍተኛ አስተዋፅዖ አድርጓል ለዚህ ግድብ መሳካት። አብዛኛውን ተቋሙ [ኤሌክትሪክ ኃይል] ተበድሮ ሲሠራ የነበረው ከንግድ ባንክ በመበደር ነው። ያን ብድር ዕዳ መክፈል ባለመቻላችን መንግሥት እንዳላ የተቋሙን ወደ 260 ቢሊየን ብር አጠቃላይ የተቋሙን ዕዳ ሲወስድ ወደ መንግሥት ዞሯል። ስለዚህ ግድቡ የተገነባው በመንግሥት ነው።"

የግድቡ የመመረቂያ ጊዜከተገለፀ ጀምሮ በግብጽ በኩል "እክል የመፍጠር" እንቅስቃሴ መኖሩንም የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አሥፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ ተናግረዋል።

በዓመቱ ለኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ወይም ለሀገር ውስጥ ፍጆታ እና ለውጭ (ለኬንያ እና ለጅቡቲ) ገበያ ከቀረበ የኤሌክትሪክ ኃይል ሽያጭ 75 ቢሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን ተቋሙ አስታውቋል።

ሰለሞን ሙጬ

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሰ