የአሜሪካ እና የዩክሬን ባለሥልጣናት በጅዳ ያደረጉት ውይይት ምን አፈራ?
ረቡዕ፣ መጋቢት 3 2017የዩክሬን እና ሩሲያ ጦርነትን ለማቆም አሜሪካ ለ30 ቀናት ተኩስ እንዲቆም የምታቀርበውን ምክረ ሐሳብ እንደሚቀበል የፕሬዝደንት ቮሎዶሚር ዜሌንስኪ መንግሥት አስታውቋል። የፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር በበኩሉ የደሕንነት ወይም የስለላ መረጃዎች ማጋራትን ጨምሮ አሜሪካ ለዩክሬን የምታደርገውን ወታደራዊ ዕገዛ መልሶ ለመጀመር ፈቃደኛ ሆኗል።
ሁለቱ ሀገሮች ከሥምምነት የደረሱት በሳዑዲ አረቢያ ጅዳ ከተማ ከሥምንት ሰዓታት በላይ የዘለቀ ውይይት ካደረጉ በኋላ ነው። ቀሪው ጉዳይ አሜሪካ ለ30 ቀናት ተኩስ እንዲቆም የምታቀርበውን ምክረ ሐሳብ ሩሲያ ትቀበላለች ወይ የሚለው ይሆናል።
የአሜሪካ እና የዩክሬን ባለሥልጣናት ውይይት በሳዑዲ አረቢያ እየተካሔደ ነው
የአሜሪካ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ ሀገራቸው ምክረ ሐሳቡን ለሩሲያ እንደምታቀርብ ተናግረዋል። ውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከሩሲያ በኩል አዎንታዊ ምላሽ ይጠብቃሉ።
የፕሬዝደንት ቭላድሚር ፑቲን ጽህፈት ቤት ወይም የክሬምሊን ቃል አቀባይ ዲሚትሪ ፔስኮቭ በጅዳ የተደረገውን ውይይት ውጤት የአሜሪካ ባለሥልጣናት “በሚቀጥሉት ቀናት በተለያዩ የመገናኛ መንገዶች ያሳውቁናል” ሲሉ ተናግረዋል። እሸቴ በቀለ በዚሁ ጉዳይ ላይ በዋሽንግተን የዶይቼ ቬለ ወኪል አበበ ፈለቀን በስልክ አነጋግሮታል።
አበበ ፈለቀ
እሸቴ በቀለ
ማንተጋፍቶት ስለሺ