የትግራይ ነፃነት ፓርቲ የሁለቱን የህወሓት አንጃዎች አቋም ተቃወመ
ማክሰኞ፣ ግንቦት 12 2017የህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ(ህወሓት) ሁለት አንጃዎች በየፊናቸዉ ከኢትዮጵያ እና ከኤርትራመንግሥታት ጋር ለመተባበር እየጣሩ መሆናቸዉን የትግራይ ነፃነት ፓርቲ ተቃወመ።የትግራይ ነፃነት ፓርቲ መሪዎች እንዳሉት ሁለቱ አንጃዎች ከአዲስ አበባና ከአሥመራ ጋር ለመሥራት በየፊናቸዉ የሚያደርጉት ተቃራኒ ጥረት አደገኛ ነዉ።የኢትዮጵያ የፌደራል መንግስት የፕሪቶርያውን ስምምነት በሙሉ ገቢራዊ እንደሚያደርግም ፓርቲዉ ጠይቋል።ህወሓት ውስጥ የተፈጠረው መከፋፈል ተከትሎ ሁለቱ የፓርቲው ቡድኖች አስመራ እና አዲስአበባ ካሉ ሐይሎች ጋር እየሰሩ ትግራይን ወደ ከፋ ችግር እየመሩ ነው ያለው በወቅታዊ ጉዳዮች ዙርያ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሐን መግለጫ የሰጠው የትግራይ ነፃነት ፓርቲ፥ ካለፈው ጦርነት ያላገገመችው ትግራይ በነዚህ ሐይሎች እንዲሁም ከእነሱ ጋር እየተወዳጁ ባሉ የህወሓት ሁለት ቡድኖች ምክንያት በሌላ ዙር ጦርነት ስጋት ላይ ናት ሲሉ የትግራይ ነፃነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶክተር ደጀን መዝገበ ተናግረዋል።
የትግራይ ነፃነት ፓርቲ ኢትዮጵያ ኤርትራ ገብተውበት ባለው ውጥረት ዙርያ የትግራይ የፖለቲካ ሀይሎች ገለልተኛ መሆን አለባቸው ብሎ እንደሚያምን ያስታወቀ ሲሆን፥ ትግራይ በኢትዮጵያ ሕግ አውጪ ተቋም ጨምሮ በአጠቃላይ ፌደረሽኑ ውክልና የላትም፣ ኤርትራ ደግሞ ሌላ ሀገር ነው ሲሉ 'ገለልተኛ አቋም መያዝ' ለሚል ሙግት እንደ ምክንያት አቅርቧል።
ከዚህ በተጨማሪ በቅርቡ በተገለፀው የህወሓት ከፖለቲካ ፓርቲነት መሰረዝበኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ መሰረዝ ዙርያ አስተያየታቸው የሰጡት የትግራይ ነፃነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶክተር ደጀን መዝገበ፥ የህወሓት መሰረዝ የሚያፈርሰው የሰላም ስምምነት የለም ብለዋል። የትግራይ ነፃነት ፓርቲ በትግራይ ያለው ስርዓት በመቃወም ሰፊ እንቅስቃሴ እንደሚያደርግ አስታውቋል።
ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ
ነጋሽ መሐመድ
አዜብ ታደሰ