1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ
ፖለቲካሰሜን አሜሪካ

የትራምፕ እና ዜሌኒስኪ ውዝግብ

አበበ ፈለቀ
ቅዳሜ፣ የካቲት 22 2017

ዓርብ ምሽት በኋይት ሃውስ ውስጥ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕና ም/ል ፕሬዝዳንቱ ጆዲ ቫንስ ከዩክሬይኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሜር ዜሌንስኪ ጋ ያደረጉት ዱላ ቀረሽ እሰጣገባና መጯጯህ በአሜሪካ የዲፕሎማሲ ታሪክ ውስጥ ተደርጎም ታይቶም አይታወቅም። ለወትሮው ልዩነት እንኳን ቢኖር ከካሜራ ጀርባ የሚፈታ ነው የነበረው።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4rEkJ
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕና ም/ል ፕሬዝዳንቱ ጆዲ ቫንስ እና የዩክሬይኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሜር ዜሌንስኪ
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕና ም/ል ፕሬዝዳንቱ ጆዲ ቫንስ እና የዩክሬይኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሜር ዜሌንስኪምስል፦ Jim LoScalzo/CNP/ZUMA Press/IMAGO

የትራምፕ እና ዜሌኒስኪ ውዝግብ

ዓለም በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት እየተመለከተ የተፈጠረው ክስተት ግን ሁኔታው ዋሽንግተን ለኪየቭ ልትሰጥ የምትችለውን የወደፊት ድጋፍ እጣ ፈንታ ጥርጣሬ ውስጥ ጨምሮታል።
የዩክሬይንን ማዕድን በጋራ ለመጠቀምና፣ ለቀጥዩ ሰላም መስፈን የጋራ መግባባት ላይ ለመድረስ ወደ ኋይት ሃውስ ያቀኑት የዩክሬይኑ ፕሬዝዳንት ቮለድሚር ዜሌንስኪ ያሰቡት ሳይሳካ፣ ለታሪክ የሚቀመጥ ልዩ ፖለቲካዊ እሰጣገባ ነው ያስተናገዱት።  


ዜሌንስኪ ለአሜሪካ ድጋፍ በቂ ምስጋና ባለማሳየታቸው ቅሬታቸውን ያሰሙት ትራምፕ እና ምክትል ፕሬዝዳንታቸው ጄዲ ቫንስ መውጫ መግቢያው የጠፋቸውን፣ ማጠፊያው ያጠራቸውን ዜሌኒስኪን ከሩሲያ ጋር ሊደረግ በሚችለው የሰላም ስምምነት መንገድ ላይ ቆመዋል፣ ሰላምና ስምምነትንም አይፈልጉም ብለው ከሰዋቸዋል።  የዚሌኒስኪ መሠረታዊ ጥያቄ ደግሞ ሊፈረም ከታቀደው የውድ ማዕድን የጋራ ማልማት ስምምነት ባሻገር ከአሜሪካ የሚሰጠው የሰላም ዋስትና ምንድነው፣ ደግሞም የሰላም ስምምነትን ሲጥሱ የኖሩት ፑቲንስ አሁን ቃላቸውን ለመተበቃቸው ምን መተማመኛ አለን የሚል ነበር።
እንዲህ እንዲህ እያለ የተካረረው እሰጣገባ መደማመጥ ወዳጣ ጭቅጭቅነት ተቀየረ። የሚወጡትም ቃላት፣ ከዲፕሎማሲው ጎራ፣ የአንድ ሃገር መሪ በፕሮቶኮልና በክብር ከተቀበለው የሌላ ሃገር መሪ ጋ የሚያደርገው አይነት አልበረም። “ከኛ ውጪ የምትጫወትበትም፣ የምታሸንፍበትም ካርድ የለህም” አሉ ፕሬዝዳንት ትራምፕ።  “እኔ ካርታ ጨዋታ እየተጫወትኩ አይደለም” መለሱ ዜሌኒስኪ። ትራምፕ ድምጻቸውን ከፍ አድርገው፣ “በሚልዮን በሚቆጠሩ ሰዎች ሕይወት ላይ ነው ቁማር የምትጫወተው። ከሦስተኛ የዓለም ጦርነት ጋር ቁማር የምትጫወተው” አሉ።
“እናም” አሉ ዶናልድ ትራምፕ፤ “ወይ የምትባሉትን ሰምታችሁ ትስማማላችሁ አልያም እኛ ከዚህ ጉዳይ ውስጥ እጃችንን እናወጣለን፣ እኛ ወጣን ማለት ደግሞ ጦርነቱን ብቻችሁን መጋፈጣችሁ ነው።”
ዜሌንስኪ ክፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጋ መገናኛ ብዙኃን በቀጥታ ያሰራጩት የጋለ ክርክር ማድረጋቸው፣ በትራምፕ ዘንድ አልተወደደላቸውም። የእንግሊዙና የፈረንሳይ መሪወች እንኳን ሳይቀሩ በዚህ ሳምንት ትራምፕን ሲያገኙ፣ ሙገሳና ክብር የሚወዱትን ትራምፕ እየደለሉ፣ እያሞካሹ፣  በዲፕሎማሲያዊ መንገድ የሚፈልጉትን ለማስፈጸም ሞክረዋል። የዜሌንስኪ ቀጥተኛና ግልጽ መሆን ያበሳጫቸው ትራምፕ፣ “ዜሌንስኪ ጓይት ሃውስንም ሃገራችንንም አላከበረም፣ ለሰላምም ዝግጁ አይደለም፣ ዝግጁ ሲሆን መምጣት ይችላል።” ብለዋል። እናም ተዘጋጅቶ የቀረበው የምሳ ግብዣም ሳይደረግ፣ ውይይቱም፣ ስምምነቱም፣ የጋራ መግለጫውም ተሰርዞ ዜሌንስኪ ክኋይት ሃውስ ተባረው ወዲያው ወጥተው ሄደዋል።

ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕና የዩክሬይኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሜር ዜሌንስኪ
ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕና የዩክሬይኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሜር ዜሌንስኪ ሲወዛገቡምስል፦ Saul Loeb/AFP/Getty Images


ይሂው ክስተት የመገናኛ ብዙሃን ዋና መነጋገሪያ ሆኗል። ከትራምፕ ቀንደኛ  ደጋፊወች ውስጥ አንዱ የሆኑት የሪፐብሊካኑ እንደራሴ ሊድሲ ግራም ትራንምፕን ለአሜሪካ ክብር የቆሙ፣ ዜሌንስኪን ደግሞ ክብረቢስና ለሃገራቸው ሰላም ማምጣት የማይችሉ ብለው ማጣጣል ብቻ ሳይሆን ወይ ሃሳባቸውን እንዲለወጡ አልያም ከስልጣናቸው እንዲልቁም ጠይቀዋል።
የዲሞክራቱ እንደራሴ ሴት ዊልበር ሞውልተን በበኩላቸው ዜሌኒስኪን ጀግና ትራምፕና ጄዲ ቫንስን ደግሞ ፈሪና የቭላድሚር ፑቲን አገልጋይ ውሾች ናቸው ሲሉ ተደምጠዋል።

የዩክሬይኑ ፕሬዝዳንት ቮሎዲሜር ዜሌንስኪ
ፕሬዝዳንት ቮሎዲሜር ዜሌንስኪምስል፦ Jose Luis Magana/AP Photo/picture alliance


ሌላው የዲሞካርት ፓርቲ  እንደራሴ ጃክ ሪድ ደግሞ ይሄንኑ ያልተለመደ ግብግብ "የፖለቲካ ጥቃት እና የአሜሪካ መሪነት አሳፋሪ ውድቀት" በማለት ጠርተውታል። ሁኔታውን ጭካኔ የተሞላበት ትዕይንት ሲሉ የገለጹት ሪድ ሁነቱ አሜሪካ በአለም ላይ ባላት ተሰሚነት እና አቋም ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደሚያደርስ ገልጸዋል። አያይዘውም፣ ትራምፕ እና ቫንስ አሜሪካ እምነት ሊጣልበት የማይችል፣ ቃሏን የማትጠብቅ ሃገር እንደሆነች ለወዳጅም ለጠላትም መልዕክት አስተላልፈዋል ብለዋል።
እሳቸው እንዳሉት ይሄ ክስተት ብዙወችን አስገርሟል፣ አስደንግጧል። የዩክሬይን ነገን አስግቷል። የአውሮፓን ተስፋ አጨፍግጓል። ይሄንን መጯጯህ ግጭት  እንደ ጣፍጭ የሙዚቃ ቃና ታላቅ ደስታን ተላብሰው የሚሰሙት አንድ ሰው፣ ለወትሮውም የምዕራቡ አለም መከፋፈል ጾም ጸሎታቸው የሆነው፣  የራሺያው ቭላድሚር ፑቲን ናቸው።