የቀጠለው የእስራኤል እና የኢራን ውጥረት
ቅዳሜ፣ ሰኔ 7 2017እስራኤል እና ኢራን መካከል ያለው ውጥረት በከፍተኛ ሁኔታ ቀጥሏል። ኢራን በእስራኤል በሰላማዊ አካባቢዎች ላይ የሚሳኤል ጥቃት መሰንዘሯን ከቀጠለች ቴህራን „ትጋያለች” ሲሉ ዛሬ የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትስ ዝተዋል። ሚኒስትሩ ይህን ያሉት ኢራን ሌሊቱን ወደ እስራኤል ባስወነጨፈቻቸው ሚሳኢሎችእስራኤል ውስጥ ቢያንስ ሶስት ሰዎች በመገደላቸው እና በርካቶች በመቁሰላቸው ከተነገረ በኋላ ነው። ለእስራኤል ጥቃት አፀፋ ኢራን ትናንት ማምሻውን እና ሌሊት በበርካታ ዙር የረጅም ርቀት ሚሳኤሎች ወደ እስራኤል አስወንጭፋለች።
እስራኤል ለአርብ አጥቢያ ባደረሰችው ጥቃት 78 ሰዎች መገደላቸውን እና ከ 320 በላይ መቁሰላቸውን የተባበሩት መንግሥታት የኢራን አምባሳደር አሚር ሰይድ ኢራቫኒ ተናግረዋል።
«ሴቶች እና ህጻናትን ጨምሮ አብዛኛዎቹ ሰላማዊ ሰዎች ነበሩ። ግልጽ ማድረግ የምፈልገው እስራኤል ያጠቃችው ጥበቃ የሚደረግላቸው የኒውክሌር ቦታዎችን ነው። ይህ ከኢራን ድንበር አልፎ የራዲዮ አክቲቭ አደጋን ሊፈጥር የሚችል የግድየለሽነት የወንጀል ድርጊት ነው።»ብለዋል።
ኢራን በእስራኤሉ የአርብ አጥቢያ ጥቃት 20 የኢራን ኮማንደሮች እና በጠቅላላው ዘጠኝ የኒውክሌር ሳይንሲስቶቿ መገደላቸውን ዛሬ አስታውቃለች።
የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ዛሬ ቅዳሜ አመሻሹ ላይ እንዳሉት በአርቡ ጥቃት የኢራንን የኒውክሌር መርሃ ግብር ለዓመታት ወደ ኃላ መመለስ ተችሏል።
ኢራን እስራኤል ሐሙስ ለአርብ አጥቢያ በኒውክሌር ጣቢያዎቿ ላይ ላደረሰችው ጥቃት አፀፋ፤ በበርካታ ዙር የረጅም ርቀት ሚሳኤሎች ወደ እስራኤል ዛሬ አስወንጭፋለች።
ኢራን ወደ እስራኤል ያሰወነጨፈችውን ባለስቲክ ሚሳኤል ተከትሎ በእስራኤል የከተሞች የማስጠንቀቂያ ደወሎች ተስምተዋል።
ኢራን እስካሁን በእስራኤል ላይ ለሶስት ጊዜ ያህል የበቀል ጥቃቶችን አድርጋለች።እስራኤል ከትናንቱ ጥቃት በተጨማሪ ዛሬ ቅዳሜ ማለዳ ላይም በኢራን ላይ ጥቃት ሰንዝራለች።በቴህራን መህራባድ አውሮፕላን ማረፊያ ከፍተኛ ከፍንዳታ እና ቃጠሎ መድረሱን ዘገባዎች ያሳያሉ።የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ አገራቸው አርብ ማለዳ የፈጸመችው ጥቃት የኢራን የኒውክሌር መሰረተ ልማት እና የባለስቲክ ሚሳኤል ፋብሪካዎችን ለመጉዳት ያለመ ነው ብለዋል።
እስራኤል በኢራን ትናንት በፈጸመችው ጥቃት የኢራን ከፍተኛ የጦር አዛዦችን እና የኒውክሌር ሳይንቲስቶች ተገድለዋል።የትናንቱን የእስራኤልን ጥቃት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ራይዚንግ ላየን ኦፐሬሽን' (የሚያንሰራራ አንበሳ ) ዘመቻ ብለውታል።
ፀሀይ ጫኔ
ልደት አበበ