1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የሚያዝያ 27 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ ሚያዝያ 27 2017

የፕሬሚየር ሊጉን ዋንጫ መውሰዱን ገና አራት ጨዋታዎች እየቀረው አረጋግጦ የነበረው ሊቨርፑል ትናንት በቸልሲ ብርቱ ሽንፈት ገጥሞታል ። በጀርመን ቡንደስሊጋ ቅዳሜ ዕለት ከኤርቤ ላይፕትሲሽ ጋር ሦስት እኩል የተለያየው ባዬርን ሙይንሽን ሁለት ጨዋታዎች እየቀሩት ዋንጫውን መውሰዱን አረጋግጧል ። ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ለድል በቅተዋል ።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4txRN
የጀርመን ቡንደስሊጋ በከፊል ። ፎቶ፦ ከማኅደር
የጀርመን ቡንደስሊጋ በከፊል፦ ቦሩስያ ዶርትሙንድ ከቮልፍስቡርግ ጋር በተጫወተበት ወቅት ። ፎቶ፦ ከማኅደርምስል፦ Fabian Friese/Eibner/IMAGO

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

የፕሬሚየር ሊጉን ዋንጫ መውሰዱን ገና አራት ጨዋታዎች እየቀረው አረጋግጦ የነበረው ሊቨርፑል ትናንት በቸልሲ ብርቱ ሽንፈት ገጥሞታል ። በደረጃ ሠንጠረዥ ተከታዩ አርሰናልም በገዛ ሜዳው ኤሚሬትስ ስታዲየም በርመስን አስተናግዶ ተሸንፏል ። ማንቸስተር ዩናይትድም በብሬትፎርድ ሲሸነፍ ማንቸስተር ሲቲ ግን ድል ቀንቶታል ። በጀርመን ቡንደስሊጋ ቅዳሜ ዕለት ከኤርቤ ላይፕትሲሽ ጋር ሦስት እኩል የተለያየው ባዬርን ሙይንሽን ሁለት ጨዋታዎች እየቀሩት ዋንጫውን መውሰዱን አረጋግጧል ።

አትሌቲክስ

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሳምንቱ መጨረሺያ በተለያዩ የዓለም መድረኮች ለድል በቅተዋል ። በሚያሚ ግራንድ ስላም የሴቶች ፉክክር ፍሬወይኒ ኃይሉ አሸንፋለች ። በረጅም ርቀት አትሌት ሂሩት መሸሻ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች ። በ1500 ሜትር አንደኛ የወጣችው አትሌት ፍሬወይኒ በ800 ሜትር በተካሄደው ውድድር ሦስተኛ በመውጣት ስድስት ነጥብ በማግኘት በአጠቃለይ በ18 ነጥብ የአጭር ርቀትን አሸንፋለች ።

ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ለሚ ብርሃኑ እና ብርቱካን ወልዴም ቼክ ሪፑብሊክ ዋና ከተማ  ፕራግ ውስጥ ትናንት በተካሄደው የማራቶን ውድድር  በየዘርፋቸው አሸናፊ ሁነዋል ። በወንዶች ማራቶን ውድድር አትሌት ለሚ ብርሃኑ 2:05.14 በመግባት ለድል በቅቷል ። በሴቶች ማራቶን ውድድር አትሌት ብርቱካን ወልዴ 2:20.55 በመሮጥ በአንደኝነት አሸናፊ ሁናለች ። 

በሻንጋይ የዳይመንድ ሊግ ውድድር በወንዶች 5000 ሜትር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከአንድ እስከ ሦስት ተከታትለው በመግባት አሸናፊ ሁነዋል ። አትሌት በሪሁ አረጋዊ በ12:50.45 አንደኛ፤ አትሌት ኩማ ግርማ 12:50.69 ሁለተኛ፤ እንዲሁም አትሌት መዝገቡ ስሜ በ12:51.86  ሦስተኛ ደረጃ አግኝተዋል ። በሴቶች 800 ሜትር ደግሞ አትሌት ጽጌ ዱጉማ  1 ደቂቃ 56.64 ሰከንድ በመሮጥ አሸናፊ ሁናለች ። የሚያዝያ 20 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል ተብሎ የነበረው 54ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፉክክር በመሮጫ መም ችግር የተነሳ የመወዳደሪያ ቦታ እንደሚቀየር ተገልጧል ። ለመሆኑ በጥቂት ቀናት ውስጥ ይስተካከላል የተባለው የመሮጪያ ቦታ ለበርካታ ወራት ሳይቀየር እንደውም ከበፊቱ በባሰ ሁኔታ ላይ የተገኘውለምን ይሆን? የኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 ኢትዮ ስፖርት አዘጋጅ እና አቅራቢ ምሥጋናው ታደሰ ።

የኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 ኢትዮ ስፖርት አዘጋጅ እና አቅራቢ ምሥጋናው ታደሰ
የኢትዮ ኤፍ ኤም 107.8 ኢትዮ ስፖርት አዘጋጅ እና አቅራቢ ምሥጋናው ታደሰ የአዲስ አበባ ስታዲየም የመሮጪያ መምን እንደመለከተው ከሆነ ገና ለውድድር ዝግሁ አይደለምምስል፦ DW

እግር ኳስ

የፕሬሚየር ሊጉን ዋንጫ አስቀድሞ መውሰዱን ያረጋገጠው ሊቨርፑል በአሰልጣኝ አርኔ ስሎት ዘመን ከባዱን ሽንፈት ትናንት አስተናግዷል ። በባከነ ሰአት ኳንሳ በፈፀመው ስህተት የተገኘውን የፍፁም ቅጣት ምት ግብ ጨምሮ ቸልሲ ሊቨርፑልን 3 ለ1 አሸንፏል ። በትናንቱ ግጥሚያ እድል የራቀው የሊቨርፑሉ ተከላካይ ኳንሳ በገዛ መረቡ ላይ ሁለተኛው ግብ እንዲቆጠረም ሰበብ ነበር ። ኳሷን ከቸልሲ ጫና ለማራቅ ተከላካዪ ቫን ጂክ ሲመታ ኳንሳ ፊት ለፊት ተደርቦ በገዛ መረቡ ላይ አስቆጥሯል ።

በሜዳው ስታምፎርድ ብሪጅ ተጋጥሞ ወሳኝ ድል ያስመዘገበው ቸልሲ አሁን የሻንፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ ለመሆን እደወሉን ከፍ አድርጓል ። ቸልሲ የትናንት ድሉን ጨምሮ በሰበሰበው 63 ነጥብ ከኒውካስል ጋር በግብ ክፍያ ብቻ በመበለጥ አምስተኛ መሆን ችሏል ። የመጋቢት 29 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የቀድሞ የሊቨርፑል ተጨዋች ማይክል ኦዌን ቸልሲ ሊቨርፑል ዋንጫ መውሰዱን ካረጋገጠ በኋላ መግጠሙ ዕድለኛ ነው ብሏል ። በተለይ ከረፈት መልስ ሊቨርፑል ጫና ፈጥሮ ቢጫወትም ዋንጫውን መውሰዱን በማረጋገጡ ያን ያህል ሲታገል ዐልታየም ብሏል ። በእርግጥም ትናንት ለዋንጫ የሚጫወት ይመስል ከነበረው ቸልሲ አንፃር ሊቨርፑል ጨዋታውን ቀለል አድርጎ ታይቷል ።

ቸልሲ የፕሬሚየር ሊግ ዋንጫ ባለድል መሆናቸውን ያረጋገጡ ሁለት ቡድኖችን በማሸነፍ ታሪክ ሠርቷል ። ቸልሲ ከ12 ዐመት በፊትም የዋንጫ ባለድል መሆኑን ያረጋገጠው ማንቸስተር ዩናይትድን አሸንፎ ነበር ። ዋንጫውን መውሰዳቸውን አስቀድመው ካረጋገጡ በኋላ ሽንፈት ከደረሰባቸው ቡድኖች መካከል ደግሞ የሊቨርፑል የትናንት ሽንፈት አራተኛው መሆኑ ነው ።

አርሰናል በሜዳው ተጫውቶ በበርመስ የ2 ለ1 ሽንፈት ገጥሞታል ። ዌስትሀም ዩናይትድ እና ቶትንሀም አንድ እኩል ተለያይተዋል ። ማንቸስተር ዩናይትድ በብሬንትፎርድ 4 ለ3 ተሸንፏል ። በአንጻሩ ማንቸስተር ሲቲ ዎልቭስን 1 ለ0 አሸንፏል ። ዛሬ ማታ ክሪስታል ፓላስ ከኖቲንግሀም ፎረስት ጋር ይጋጠማሉ ።

በ2019 የሻምፒዮንስ ሊግ ባለድል የሆነው ሊቨርፑል ዘንድሮ በፕሬሚከር ሊጉ ግን ዋንጫውን ከወዲሁ መውሰዱን አረጋግጧል
በ2019 የሻምፒዮንስ ሊግ ባለድል የሆነው ሊቨርፑል ዘንድሮ ከሻምፒዮንስ ሊጉ ቢሰናበትም በፕሬሚከር ሊጉ ግን ዋንጫውን ከወዲሁ መውሰዱን አረጋግጧልምስል፦ Actionplus/picture alliance

ሊቨርፑል፣ አርሰናል፣ ማንቸስተር ሲቲ፣ ኒውካስል እና ቸልሲ የሻምፒዮንስ ሊግ ከአንደኛ እስከ አምስተኛ ደረጃን ይዘዋል ። ኢፕስዊች ታወን፣ ላይስተር ሲቲ እና ሳውዝሀምፕተን ወራጅ መሆናቸው ተረጋግጧል ።

አሌክሳንደር አርኖል ከልጅነት ቡድኑ ሊቨርፑል ሊለይ መሆኑ ይፋ ሁኗል፤ ምናልባትም ለሪያል ማድሪድ ሊጫወት ይችል ይሆናል ተብሏል ። የባዬርን ሌቨርኩሰን አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ ከሁለት ዓመት ከመንፈቅ የስኬት ቆይታ በኋላ ከቡንደስሊጋው ሊለይ መሆኑ ተገልጧል ። ወደ አገሩ ስፔን አቅንቶም ሪያል ማድሪድን ሊያሰለጥን ይችል ይሆናል ተብሏል ። እንደተባለው አሌክሳንደር አርኖልድ እና ዣቪ አሎንሶ ወደ ሪያል ማድሪድ የሚያቀኑ ከሆነ የቀድሞው የሊቨርፑል ተጨዋቾች በአንድ ቡድን በአሰልጣኝ እና ተጨዋችነት ይከሰታሉ ማለት ነው ። የመጋቢት 22 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

በጀርመን ቡንደስሊጋ ቅዳሜ ዕለት በኤርቤ ላይፕትሲሽ ሜዳ ተጋጥሞ ሦስት እኩል የተለያየው ባዬርን ሙይንሽን ዋንጫውን መውሰዱን አረጋግጧል ። ባዬርን ሙይንሽን፣ ባዬር ሌቨርኩሰን፣ አይንትራኅት ፍራንክፉርት እና ፍራይቡርግ ለአውሮጳ ሻምፒዮንስ ሊግ ከአንደኛ እስከ አራተኛ ቦታ ይዘዋል ። ቦሩስያ ዶርትሙንድ በአምስተኛ ደረጃ የአውሮጳ ሊግ ተሳታፊ ቦታን ይዟል ። ኤርቤ ላይፕትሲሽ በበኩሉ የአውሮጳ ሊግ የደርሶ መልስ ተጋጣሚ ቦታን ይዟል ። የነጥብ ልዩነቶቹ ተቀራራቢ በመሆናቸው ደረጃዎቹ ሊቀያየሩ ይችላሉ ። ሆልሽታይን ኪዬል እና ቦሁም ወራጅ ቀጣና ውስጥ ይገኛሉ ሐይድንሀይም ወራጅ ቀጣናው ግርጌ ከሁለቱ ቡድኖች በቅርብ ርቀት መገኘቱ የነዚህ ቡድኖች ቀጣይ ጨዋታዎችን አጓጊ ያደርገዋል።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

 

ማንተጋፍቶት ስለሺ ሥዩም Mantegaftot Sileshi ዜና አዘጋጅ፤ መርኃ ግብር መሪ፤ የሳምንታዊ ስፖርት አዘጋጅ ነው፥ በአጭር ፊልም የበርካታ ዓለም አቀፍ ተሸላሚው ማንተጋፍቶት የቪዲዮ ዘገባዎችንም ያዘጋጃል።@manti