1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የመጋቢት 8 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ መጋቢት 8 2017

በደቡብ ኮሪያ የሴዑል ማራቶን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በወንድም በሴትም አሸናፊ ሁነዋል ። በባርሴሎና ማራቶንም ድል ተገኝቷል ። በእንግሊዝ የካራባዎ ዋንጫ የፍጻሜ ግጥሚያ ኒውካስትል ትናንት በአሌክሳንደር ኢሳቅ ወሳኝ ግብ ሊቨርፑልን አሸንፏል ። አርሰናል በለንደን ደርቢ ቸልሲን አሸንፏል ። ላይፕትሲሽ ዶርትሙንድን 2 ለ0 ኩም አድርጓል ።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4rtgo
Fußball Bundesliga 2025 | RB Leipzig vs. Borussia Dortmund | Peter Gulasci
ምስል፦ Lisi Niesner/REUTERS

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

በደቡብ ኮሪያ የሴዑል ማራቶን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በወንድም በሴትም አሸናፊ ሁነዋል ። በባርሴሎና ማራቶንም ድል ተገኝቷል ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ግጥሚያ ልምምዱን ዛሬ አድርጓል ። ቃለ መጠይቅ ይኖረናል ። ኢትዮጵያ በሴቶች ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ማጣርያ ሳታልፍ ቀርታለች ።

በእንግሊዝ የካራባዎ ዋንጫ የፍጻሜ ግጥሚያ ኒውካስትል ትናንት በአሌክሳንደር ኢሳቅ ወሳኝ ግብ ሊቨርፑልን አሸንፏል ። ፌዴሪኮ ኪዬሳ በጨዋታው ፍጻሜ ለሊቨርፑል የመጽናኛውን ግብ አስቆጥሯል ። ከሻምፒዮንስ ሊግ ለተሰናበተው ሊቨርፑል አሁን የቀረው አንድ እድል የፕሬሚየር ሊጉ ዋንጫ ነው ። ተከታዩ አርሰናል በለንደን ደርቢ ቸልሲን አሸንፏል ። በጀርመን ቡንደስሊጋ የመሪው ባዬርን ሙይንሽን ነጥብ መጣል ለተከታዬ ባዬር ሌቨርኩሰን መልካም አጋጣሚ ሁኗል ።  ዶርትሙንድ ዳግም ሽንፈት ገጥሞታል ።

አትሌቲክስ

ደቡብ ኮሪያ ውስጥ ትናንት (መጋቢት 07 ቀን፣2017 ዓ.ም) በተካሄደው የሴኡል ማራቶን በሁለቱም ፆታ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች አሸናፊ ሁነዋል ። በተለይ በሴቶች ፉክክር፦ ኢትዮጵያውያቱ አትሌቶች ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ተከታትለው በመግባት ብቃታቸውን ዐሳይተዋል ። በውድድሩ፦ አትሌት በቀለች ጉደታ (2:21.36) አንደኛ፣አትሌት ፍቅርተ ወረታ ሁለተኛ (2:22.54) እንዲሁም አትሌት መስታወት ፍቅር ሦስተኛ (2:23.10) ደረጃውን በመጠቅለል በተከታታይ ገብተዋል ።

በወንዶች ተመሳሳይ ርቀት ፉክክር፦ ኢትዮጵያዊው አትሌት ሀፍቱ ተክሉ (2:05:42) ከኬንያውያን አንገት ለአንገት ተናንቆ በአንደኛነት አሸንፏል ። ኬንያውያኑ ፌሊክስ ኪርዋ እና በርናርድ ኪፕሮፕ ኮይች ከሀፍቱ በሁለት እና በስምንት ሰከንድ ልዩነት የሁለተኛ እና የሦስተኛ ደረጃ አግኝተዋል ። በዘንድሮው የሴኡል ማራቶን ከሰባት አገራት የተውጣጡ 170 አትሌቶች በአጠቃላይ ከ66 አገራት 40,000 ተሳታፊዎች ተገኝተዋል ። የመጋቢት 01 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ትናንት ስፔን ውስጥ በተከናወነው የባርሴሎና ማራቶንም ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ድል ቀንቷቸዋል ። በወንዶች ፉክክር አትሌት ተስፋዬ ድሪባ ከበርካታ ኬንያውያን ተፎካካሪዎች መሀከል (02:04:13) አንደኛ በመውጣት ሲያሸንፍ፤ በሴቶች ፉክክር አትሌት የብርጓል መለሠ(02:20:47) ሁለተኛ ደረጃ አግኝታለች ። ኬኒያዊቱ ሻሮን ቼሊሞ (02:19:33)በመሮጥ በአንደኛነት አሸንፋለች ። በወንዶች ፉክክር፦ ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶችት መኳንንት ዐየነው 6ኛ እንዲሁም ካሳሁን ኃይሉ 10ኛ ከማጠናቀቃቸው ውጪ ኬንያውያን ከ2ኛ እስከ 9ኛ በመግባት አሸናፊ ባይሆኑም ብርታታቸውን ዐሳይተዋል ። 

በሴዑል ማራቶን ኢትዮጵያውያን በወንድም በሴትም አሸናፊ ሁነዋል፥ በባርሴሎና ማራቶንም ድል ተገኝቷል
ደቡብ ኮሪያ የሴዑል ማራቶን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በወንድም በሴትም አሸናፊ ሁነዋል፥ በባርሴሎና ማራቶንም ድል ተገኝቷል ምስል፦ Pavel/Pond5 Images/IMAGO

እግር ኳስ

የኒውካስትል ቡድን ከ70 ዓመታት ወዲህ የአገር ውስጥ ዋንጫን በእጁ አስገብቷል ። ቡድኑ ላለፉት 55 ዓመታት ሲመኘው የነበረውን ታላቅ ውጤት አስመዝግቧል ። ትናንት በነበረው የካራባዎ የፍጻሜ ግጥሚያ ሊቨርፑልን 88,513 ሰዎች በታደሙመበት የዌምብሌ ስታዲየም 2 ለ1 በማሸነፍ ዋንጫውን ወስዷል ።

ለኒውካስትል ቀዳሚዋን ግብ የመጀመሪያው አጋማሽ መደበኛ ክፍለ ጊዜ ሲጠናቀቅ በ45ኛ ደቂቃ ላይ ያስቆጠረው ዳን በርን ነው ። አሌክሳንደር ይሣቅ ደግሞ ከረፍት መልስ በ52ኛው ደቂቃ ላይ ሁለተኛዋን አስቆጥሯል ። መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በጭማሪው አራተኛ ደቂቃ ላይ ፌዴሪኮ ኪዬሳ ለሊቨርፑል የማስተዛዘኛዋን ግብ በማግባት ቡድኑን በዜሮ ከመሸነፍ ቢታደግም፤ ኒውካስትሎች የትናንቱን ጨዋታ ማሸነፋቸው በእርግጥም የሚገባቸው ነበር ። የየካቲት 24 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የሊቨርፑል አሰልጣኝ አርኔ ስሎት የትናንቱን የዋንጫ ፍጻሜ ጨዋታ በተመለከተ ተጠይቀው ሲመልሱ፦ «አናዳጅ ውጤት፤ የሚያበሳጭ እንቅስቃሴ» ሲሉ በቡድናቸው መናደዳቸውን አልሸሸጉም ። ባለፉት ውድድሮች ከኤፍ ኤ ካፕ እና ከሻምፒዮንስ ሊግ ፉክክር ለተሰናበተው ሊቨርፑል የትናንቱ ውጤት በእርግጥም ለአሰልጣኙ እጅግ የሚያበሳጭ ነበር ።

ፕሬሚየር ሊግ

በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊጉ 29 ጨዋታዎች ሊቨርፑል ዋንጫ የማግኘት እድሉን አስፍቶ 70 ነጥብ ሰብስቧል ። አርሰናል ትናንት ቸልሲን በለንደን ደርቢ ገጥሞ በሚኬል ሜኒኖ 20ኛ ደቂቃ ላይ በተቆጠረች ብቸኛ ግብ አሸንፏል ። ነጥቡንም ወደ 58 ከፍ በማድረግ ከሊቨርፑል በ12 ነጥብ ርቀት ተጠግቷል ። ሊቨርፑል ከቀሪ ጨዋታዎቹ በአራቱ ካልተሸነፈ በቀር አርሰናልም ሆነ በ54 ነጥብ በሦስተኛ ደረጃ የሚከተለው ኖቲንግሀም ፎረስት ዋንጫውን የማንሳት እድል የላቸውም ። ከተለያዩ የዋንጫ ፉክክሮች የተሰናበተው ሊቨርፑል በእጁ ለማስገባት ሰፊ ዕድል ያለውን የፕሬሚ,ር ሊግ ዋንጫ እንዲህ በቀላሉ አሳልፎ ይሰጣል ማለት ይከብዳል፥ የኳስ ነገር ግን ዐይታወቅም ። 

አርሰናል ትናንት ቸልሲን በለንደን ደርቢ ገጥሞ በሚኬል ሜኒኖ 20ኛ ደቂቃ ላይ በተቆጠረች ብቸኛ ግብ አሸንፏል
አርሰናል ትናንት ቸልሲን በለንደን ደርቢ ገጥሞ በሚኬል ሜኒኖ 20ኛ ደቂቃ ላይ በተቆጠረች ብቸኛ ግብ አሸንፏል ምስል፦ Jacques Feeney/Offside/IMAGO

ትናንት በነበሩ የፕሬሚየር ሊግ ግጥሚያዎች የተሸነፈው ቸልሲ በ49 ነጥብ የአራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። ኢፕስዊች ታወንን ቅዳሜ ዕለት በሜዳው 4 ለ2 ድል ኩም ያደረገው ኖቲንግሀም ፎረስት በ54 ነጥብ በደረጃ ሰንጠረዡ ሦስተኛ ነው ። ከትናንት በስትያ ብራይተንን በሜዳው ኢቲሀድ ስታዲየም ጋብዞ አንድ እኩል የተለያየው ማንቸስተር ሲቲ በ48 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ሰፍሯል ። ትናንት ሊቨርፑልን በካራባዎ ዋንጫ ያሸነፈው ኒውካስትል ከብራይተን ጋር በእኩል 47 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። ኢፕስዊች ታወን፣ ላይስተር ሲቲ እና ሳውዝሐምፕተን በተሰናባች ቀጣና ውስጥ ተደርድረዋል ።  የየካቲት 17 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ቡንደስሊጋ

ሽቱትጋርት ላይ በባከነ ሰከንድ በተቆጠረ ግብ ባዬር ሌቨርኩሰን ከመሪው ባዬርን ሙይንሽን ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ማጥበብ ችሏል ። ቦሁም ውስጥ የፍራንክፉርት ነውጠኛ ደጋፊዎች ጨዋታው በሰአቱ እንዳይጀምር መሰናክል ሁነዋል ። በቡንደስሊጋ ታሪክ ላለፉት 15 ዓመታት በሜዳቸው ባሼር ሌቨርኩሰንን ማሸነፍ የተሳናቸው ሽቱትጋርቶች ትናንት  የቆየ ታሪካቸውን የሚያድሱ መስለው ነበር ። ቀዳሚዎቹን ሁለት ግቦች በማስቆጠር ሽቱትጋርት ከረፍት መልስም 2 ለ0 እየመራ ነበር ። በ62ኛው ደቂቃም ሌቨርኩሰን 3 ለ1 እየመራ ነበር ። ብዙም አልቆየ ጨዋታው ወደ 3 ለ2 ሲቀየር ። የማታ ማታ የበረቱት ባዬር ሌቨርኩሰኖች በስተመጨረሻ መደበኛ 90 ደቂቃ ተጠናቆ በጭማሪው ፓትሪክ ሺክ ባስቆጠራት ግብ ሽቱትጋርትን በሜዳው 4 ለ3 አሸንፈዋል ። 

ባዬር ሌቨርኩሰን የማታ ማታ ሽቱትጋርትን በሜዳው 4 ለ3 አሸንፏል
ባዬር ሌቨርኩሰን በጨዋታው ፍጻሜ ሽቱትጋርትን በሜዳው 4 ለ3 አሸንፏልምስል፦ Harry Langer/dpa/picture alliance

በዚህም መሠረት፦ ባዬር ሌቨርኩሰን ነጥቡን ወደ 56 ከፍ አድርጎ ከመሪው ባዬርን ሙይንሽን በስድስት ነጥብ ብቻ መራቅ ችሏል ።  ከፍራይቡርግ ጋር ሁለት እኩል የተለያየው ማይንትስ በ45 ነጥብ 3ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል ። በቦሁም ሜዳ የ3 ለ1 ድል የቀናው  አይንትራኅት ፍራንክፉርት በተመሳሳይ 45 ነጥብ ሁኖም በግብ ክፍያ 4ኛ ደረጃ ላይ ሰፍሯል ። 42 ነጥብ ሰብስቦ 5ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ላይፕትሲሽ ዶርትሙንድን 2 ለ0 ኩም አድርጓል ። ቦሩስያ ዶርትሙንድ በ35 ነጥቡ ደረጃው 11ኛ ነው ። ቦሁም በ20 ነጥብ 16ኛ ወራጅ ቀጣና ግርጌ ላይ ይገኛል ። ሐይደንሀይም ከበታቹ 18ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ሆልሽታይን ኪዬልን ትናንት 3 ለ1 አሸንፎ በደረጃው ቦታ ተቀያይሯል ። ሆኖም ሁለቱም 17 እና 19 ነጥብ ብቻ ይዘው ወራጅ ቀጣናው ውስጥ ይገኛሉ ።  የየካቲት 10 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ 

የኢትዮጵያ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች የእግር ኳስ ቡድን በዓለም ዋንጫ ወደ መጨረሻው ማጣርያ ሳያልፍ ቀርቷል ። አዲስ አበባ አበበ ቢቂላ ስታዲየም ውስጥ ቅዳሜ ዕለት በነበረው ሁለተኛ ዙር የመልስ ጨዋታ ከካሜሩን ጋር የገጠመው የኢትዮጵያ ቡድን የ1 ለ0 ሽንፈት አስተናግዶ ሳያልፍ ቀርቷል ። በደርሶ መልስ ድምር ውጤት የካሜሩን ቡድን 6 ለ2 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር አልፏል ። 

የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ቡድን

የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ቡድን ዋሊያዎቹ ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ከግብጽ እና ከጅቡቲ ጋር ለሚኖራቸው ግጥሚያ ዛሬ በአዲስ አበባ ስታዲየም ልምምድ አድርገዋል ። የስፖርት ጋዜጠኛ ዖምና ታደለ በቦታው ተገኝቶ ነበር ።  የዛሬው ልምምድ በሁለት መልኩ የተከፈለ እንደነበር ገልጧል ። 

የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ቡድን ተጨዋቾች በአዲስ አበባ ስታዲየም ሲለማመዱ
የኢትዮጵያ የእግር ኳስ ቡድን ተጨዋቾች በአዲስ አበባ ስታዲየም ሲለማመዱምስል፦ Omna Tadel/DW

ዖምና አንደኛው ልምምድ በመከላከል እና መልሶ ማጥቃት ላይ ያተኮረ ልምምድ መሆኑን ጠቅሷል ።  በሁለተኛው የልምምድ ምእራፍም ቡድኑ በሁለት ተከፍሎ በመከላከል ላይ ያተኮረ ጨዋታ ሲያሠሩ መመልከቱን ጠቅሷል ። ዖምና በቦታው ተገንቶ እንደተመለከተው ከሆነ ስታዲየሙ «በአጭር ጊዜ ውስጥ ተሠርቶ» ይጠናቀቃል የሚለው በተግባር የታየ አለመሆኑ ታውቋል ። እንደውም የሜዳው ሣር ውኃ ከማጣት የተነሳ በሚመስል ወይቦ ወደ ቢጫነት ተቀይሯል፥ የመሮጫ መሙም ጭራሽ የነበረውም ተነስቷል ።

የጀርመን ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን

አሰልጣኝ ዩሊያን ናግልስማን የባዬርን ሙይንሽን አማካይ ተጫዋች ሌዎን ጎሬትርስካን የጀርመን ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድንን እንዲቀላቀል ባለፈው ሣምንት ጥሪ አስተላልፈዋል ።  ብሔራዊ ቡድኑ በአውሮጳ ኔሽንስ ሊግ ለሩብ ፍጻሜ ከጣሊያን ጋር የደርሶ መልስ ግጥሚያ አለው ።  የየካቲት 3 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የ30 ዓመቱ ሌዎን ጎሬትስካ እንደ ጎርጎሪዮስ አቆጣጠር ከ2023 ጀምሮ ለብሔራዊ ቡድኑ አልተሰለፈም ። ጀርመን ያሰናዳችው የዩሮ 2024 የአውሮጳ እግር ኳስ ግጥሚያ ላይ አልነበረም ። ለሌዎን ጎሬትስካ አሰልጣኙ ጥሪ ያስተላለፉት ሐሙስ ዕለት ነው ። ከጣሊያን ጋር የደርሶ መልስ ግጥሚያው የፊታችን ሐሙስ እና እሁድ ይካሄዳል ።

አሰልጣኝ ዩሊያን ናግልስማን ለሌዎን ጥሪውን ያስተላለፉት በርካታ ተጨዋቾቻቸው ገሚሱ በመጎዳቱ እና በመታመሙ ነው ተብሏል ። ካይ ሐቫርትስ፣ ፍሎሪያን ቪርትስ፣ ማትክ-አንድሬ ተር ስቴገን፣ ኒክላስ ፉይክሩግ፣ ቤንጃሚን ሔንሪሽስ እና አሌክሳንዳር ፓቭሎቪች ጎዳት ከደረሰባቸው አለያም ከታመሙት መካከል ይገኙበታል ።

የጀርመን ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን አሰልጣኝ ዩሊያን ናግልስማን የ
የጀርመን ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን አሰልጣኝ ዩሊያን ናግልስማን የባዬርን ሙይንሽን አማካይ ተጫዋች ሌዎን ጎሬትርስካ (ነጭ የለበሰው) ደረቱን በእጃቸው ደገፍ አድርገው ሲያዋሩትምስል፦ Ulrich Hufnagel/picture alliance

የጀርመን ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን የጣሊያን አቻውን በሩብ ፍጻሜው የሚያሸንፍ ከሆነ ሙይንሽን እና ሽቱትጋርት ውስጥ በሚካካሄዱየግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ተሳታፊ ይሆናል ።  ሁለቱ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ለረቡዕ፤ ግንቦት 27 እና በነጋታው ቀጠሮ ተይዞላቸዋል ። የፍጻሜ ግጥሚያው እሁድ ሰኔ 1 ቀን፤ 2017 ዓ.ም ቱሪን ጣሊያን ውስጥ ይካሄዳል ። የጥር 26 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ፎርሙላ አንድ

በአውስትራሊያ ግራንድ ፕሪ የፎርሙላ አንድ ሽቅድምድም፦ ሌዊስ ሐሚልተን በፌራሪ ተሽከርካሪው በ7ኛ ደረጃ አጠናቀቀ ። የማክላረኑ አሽከርካሪ ላንዶ ኖሪስ የትናንቱን ሽቅድምድም አሸንፎ 25 ነጥብ አግኝቷል ። በአንጻሩ ሌዊስ ሐሚልተን ያገኘው አንድ ነጥብ ብቻ ነው ። የሬድ ቡል አሽከርካሪው ማክስ ፈርሽታፐን ሁለተኛ በማጠናቀቅ 18 ነጥብ አግኝቷል ። የመርሴዲሱ ጆርጅ ሩሴል ሦስተኛ በመውጣት 15 ነጥብ አግኝቷል ።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

አዜብ ታደሰ

 

ማንተጋፍቶት ስለሺ ሥዩም Mantegaftot Sileshi ዜና አዘጋጅ፤ መርኃ ግብር መሪ፤ የሳምንታዊ ስፖርት አዘጋጅ ነው፥ በአጭር ፊልም የበርካታ ዓለም አቀፍ ተሸላሚው ማንተጋፍቶት የቪዲዮ ዘገባዎችንም ያዘጋጃል።@manti