1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

የመጋቢት 15 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

ሰኞ፣ መጋቢት 15 2017

በቻይና ናንጂንግ የዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ፉክክር ኢትዮጵያ ዩናይትድ በ3ተኛ ደረጃ አጠናቃለች ። በግብጽ የ2 ለ0 ሽንፈት ያስተናገደው የኢትዮጵያ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ከጅቡቲ ጋር ዛሬ ማታ ይጋጠማል ። በአውሮጳ የኔሽንስ ሊግ ጀርመን ከፖርቹጋል ሙይንሽን አሬና ውስጥ፤ ስፔን ከፈረንሳይ ጋር ደግሞ ሽቱትጋርት አሬና ውስጥ ይጋጠማሉ ።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4sByL
በ1500 ሜትር ርቀት ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጉዳፍ ጸጋዬ በ(3:54.86)ሮጣ ስታጠናቅቅ ክብረወሰን ጭምር በመስበር  ነበር ።  አትሌት ድርቤ ወልተጂ ጉዳፍን ተከትላ በመግባት የብር ሜዳሊያ አስገኝታለች
በ1500 ሜትር ርቀትም ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጉዳፍ ጸጋዬ በ(3:54.86)ሮጣ ስታጠናቅቅ ክብረወሰን ጭምር በመስበር  ነበር ። የአገሯ ልጅ አትሌት ድርቤ ወልተጂ ጉዳፍን ተከትላ በመግባት የብር ሜዳሊያ አስገኝታለች ምስል፦ Dar Yasin/AP/picture alliance

ሣምንታዊ የስፖርት ዘገባ

በቻይና ናንጂንግ ከተማ የዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ፉክክር  ኢትዮጵያ  ዩናይትድ ስቴትስ እና ኖርዌይን ተከትላ በሦስተኛ ደረጃ አጠናቃለች ። Ethiopiaበግብጽ የ2 ለ0 ሽንፈት ያስተናገደው የኢትዮጵያ ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ከጅቡቲ ጋር ዛሬ ማታ ሞሮኮ ውስጥ ይጋጠማል ። በአውሮጳ የኔሽንስ ሊግ እግር ኳስ በግማሽ ፍጻሜው ጀርመን ከፖርቹጋል ሙይንሽን አሬና ውስጥ፤ ስፔን ከፈረንሳይ ጋር ደግሞ ሽቱትጋርት አሬና ውስጥ ይጋጠማሉ ። 

አትሌቲክስ

ቻይና ናንጂንግ ከተማ ውስጥ ትናንት (መጋቢት 14 ቀን፣2017 ዓ.ም) በተጠናቀቀው የዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ፉክክር ኢትዮጵያ ብሪታንያ እና ጣሊያንን አስከትላ ከዓለም በ3ኛ ደረጃ አጠናቃለች ። ኢትዮጵያ በሜዳሊያ ሠንጠረዥ ከዩናይትድ ስቴትስ እና ኖርዌይ ቀጥላ በሁለት የወርቅ እና ሦስት የብር ሜዳሊያዎች የሦስተኛ ደረጃ አግኝታለች ።  ለኢትዮጵያ ከተገኘው አምስት ሜዳሊያዎች ውስጥ በአትሌት በሪሁ ኃይሉ ከተገኘው የብር ሜዳሊያ በስተቀር የተቀሩት በአጠቃላይ በሴት አትሌቶቻችን የተገኙ ናቸው ። ሁለቱን የወርቅ ሜዳሊያዎች ያስገኙት ኢትዮጵያውያት አትሌቶች ፍሬወይኒ ኃይሉ እና ጉዳፍ ጸጋዬ ናቸው ። 

በሴቶች የ3000 ሜትር ርቀት ፍጻሜ አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ ድል ተጎናጽፋ የወርቅ ሜዳሊያ ለማጥለቅ የፈጀባት ጊዜ (8:37.21)ነው ። ብርቱ ፉክክር በታየበት የ3000 የፍጻሜ ሩጫ፦ ሜትር አሜሪካዊቷ ሼልቢ ሁሊሃን ፍሬወይኒ ኃይሉን በአንድ ነጥብ አምስት ሰከንድ ተከትላ ሁለተኛ ወጥታለች ። የአውስትራሊያዋ ሯጭ ጄሲካ ሁል ከሼልቢ በሁለት ማይክሮ ሰከንድ ተበልጣ ነው ሦስተኛ የወጣችው ። በዚህ ውድድር ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ብርቄ ኃየሎም አሜሪካዊቷ ዊትኒ ሞርጋንን ተከትላ የአምስተኛ ደረጃ አግኝታለች ።

በ1500 ሜትር ርቀትም ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት አትሌት ጉዳፍ ጸጋዬ  በ(3:54.86) ሮጣ ስታጠናቅቅ ክብረወሰን ጭምር በመስበር  ነበር ። የአገሯ ልጅ አትሌት ድርቤ ወልተጂ ጉዳፍን ተከትላ በመግባት የብር ሜዳሊያ አስገኝታለች ። አትሌት ድርቤ ወልተጂ ከጉዳፍ በአራት ነጥብ ዐርባ አራት ሰከንድ ተከትላ በመግባት (3:59.30) የብር ሜዳሊያ አስገኝታለች ። ብሪታንያዊቷ አትሌት ጆርጂያ ሁንተር ቤል ሦስተኛ በማጠናቀቅ የነሐስ ሜዳሊያ ተሸላሚ ሁናለች ።

በ1500 ሜትር ርቀት ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጉዳፍ ጸጋዬ ውድድሩን ስትመራ
በቻይና ናንጂንግ ከተማ የዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ፉክክር በ1500 ሜትር ርቀት ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ጉዳፍ ጸጋዬ ውድድሩን ስትመራምስል፦ Dar Yasin/AP/picture alliance

የኢትዮጵያ አመርቂ ድል

በወንዶች የ3000 ሜትር የፍጻሜ ሩጫ ደግሞ ኢትዮጵያዊው አትሌት በሪሁ አረጋዊ (7:46.25)በመሮጥ የብር ሜዳሊያ አስገኝቷል ።  ኖርዌያዊው አትሌት ጄኮብ ኢንገርብሪግስተን በሪሁን ቀድሞ የወርቅ ሜዳሊያ ያጠለቀው ከአንድ ሰከንድ ባነሰ 16 ማይክሮ ሰከንድ ለጥቂት ቀድሞ ነው ። የአውስትራሊያው ኪይ ሮቢንሰን ሦስተኛ ደረጃ ሲያገን፥ አንደኛ ከወጣው ኖርዊያዊ አትሌት የተቀደመው በአንድ ሰከንድ ብቻ ነበር ። ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ቢንያም መሐሪ እና ጌትነት ዋለ ኤርትራዊው ዳዊት ሠዓረን ከመሀል አድርገው 9ኛ እና 11ኛ ደረጃ በመያዝ አጠናቅቀዋል ። የጀርመኑ ሣም ፓርሶናስ 12ኛ ደረጃ አግኝቷል ።

በትናንትናው የ800 ሜትር የሴቶች የፍጻሜ ውድድር አትሌት ንግሥት ጌታቸው ሁለተኛ በመሆን ለኢትዮጵያ ተጨማሪ የብር ሜዳሊያ አስገኝታለች ። የገባችበት (1:59.63) የግሏ ምርጥ ሰአት ሁኖ ተመዝግቧል ።  በውድድሩ ከፍተኛ ቅድመ ግምት አግኝታ የነበረው የአምና ሻምፒዮና ጽጌ ዱጉማ (2:04.76) ስድስተኛ በመሆን አጠናቃለች ። የ800 ሜትር ርቀት የፍጻሜ ውድድሩን አሸንፋ (1:58.40) የወርቅ ሜዳሊያ ያጠለቀችው የደቡብ አፍሪቃዋ ሯጭ ፕሩደንስ ሴክጎዲሶ አሸንፋለች ። የፖርቹጋሏ ፓትሪሺያ ሲልቫ (1:59.80) በሦስተኛ ደረጃ የነሐስ ተሸላሚ ሁናለች ።

በአጠቃላይ የሜዳሊያ ሠንጠረዥ በአንደኛነት ያጠናቀቀችው  ዩናይትድ ስቴትስ  ናት ። 6 የወርቅ 4 የብር እና 6 የነሐስ ሜዳሊያዎች በድምሩ 16 ሜዳሊያዎችን ሰብስባለች ። ተከታዩዋ ኖርዌይ በ 3 የወርቅ እና 1 የነሐስ ሜዳሊያ በድምሩ 4 ሜዳሊያዎች ነው የሁለተኛ ደረጃ ያገኘችው ። ከአፍሪቃ የሜዳሊያ ሠንጠረዥ ውስጥ መግባት የቻሉት፦ ደቡብ አፍሪቃ እና ቡርኪና ፋሶ ብቻ ናቸው ። ደቡብ አፍሪቃ በአንድ የወርቅ እና በአንድ የነሐስ በድምሩ ሁለት ሜዳሊያዎች 11ኛ ደረጃ አግኝታ አጠናቃለች ። ቡርኪናፋሶ በአንድ ብቸኛ የነሐስ ሜዳሊያ እንደ ጀርመን ሁሉ የ27ኛ ደረጃ ይዛ አጠናቃለች ። ሉክዘምበርግ፤ ፖርቹጋል እና ዩክሬንም በአንድ የነሐስ ሜዳሊያ ደረጃቸው እንደ ቡርኪናፋሶ እና ጀርመን 27ኛ ነው ። ኬንያ ከሜዳሊያ ሰንጠረዡ ውጪ ናት ።

እግር ኳስ

ጀርመን በኔሽንስ ሊግ የእግር ኳስ ግጥሚያ ጣሊያንን በሩብ ፍጻሜው አሰናብታለች
ጀርመን በኔሽንስ ሊግ የእግር ኳስ ግጥሚያ ጣሊያንን በሩብ ፍጻሜው አሰናብታለችምስል፦ Marc Schueler/Sportpics/picture alliance

ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ሞሮኮ ውስጥ ከግብጽ ጋር ተጋጥመው 2 ለ0 የተሸነፉት ዋሊያዎቹ ዛሬ ማታ እዛው ሞሮኮ ውስጥ ከጅቡቲ ጋር ይጋጠማሉ ። ግብፅ  በ13 ነጥብ  ለዓለም ዋንጫ ማለፏን ከወዲሁ አረጋግጣለች ። በዐርቡ ግጥሚያ ሁለቱን ግቦች የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ላይ ያስቆጠሩት የሊቨርፑል አጥቂ ሞሐመድ ሣለህ እና አህመድ ሣይድ ናቸው ። እስካሁን በምጀርመንድቡ እያንዳንዱ ቡድን አምስት ጨዋታዎችን አከናውኗል ። ኢትዮጵያ በ3 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ናት ። ዛሬ የምትገጥማት ጅቡቲ በአንድ ብቸኛ ነጥብ የመጨረሻ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች ።  ሴራሊዮን በ8 ነጥብ ሦስተኛ፤ እንዲሁም ጊኒ ቢሳዎ በስድስት ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ ።

በአውሮጳ የኔሽንስ ሊግ እግር ኳስ የሩብ ፍጻሜ ፍልሚያ የጀርመን ቡድን ወደ ግማሽ ፍጻሜ አለፈ ። ትናንት ማታ በሁለተኛው አጋማሽ በጣሊያኖች ጫና የተፈጠረበት የጀርመን ቡድን ተጨዋቾች በመጀመሪያው አጋማሽ በመከላከል፥ አስጨንቆ በመጫወት እና ኳስ ሲነጠቁ በእልህ ኳሷን አስጥሎ መልሶ በመቆጣጠር ተሳክቶላቸው ነበር ። የመጀመሪያው አጋማሽ በጀርመን ቡድን 3 ለ0 መሪነት መጠናቀቁ በእርግጥም ለጀርመን ተጨዋቾች የሚገባቸው ነበር ማለት ይቻላል ።  ዶርትሙንድ ውስጥ የትናንት በመጀመሪያው አጋማሽ በመከላከልም ሆነ በማጥቃት የጀርመን ቡድን ከረዥም ዘመን በኋላ የተሳካ እንቅስቃሴ ያሳየበት ነበር ።  የመጋቢት 8 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

በሁለተኛው አጋማሽ ግን አሰልጣኝ ዩሊያን ናገልስማንም አምነው እንደተቀበሉት ቡድናቸው በመከላከል ላይ ማተኮሩ ለጥቃት ዳርጎታል ። ጣሊያኖች በአንፃሩ ተጠናክረው በማጥቃት ላይ አተኩረው ነበር ወደ ሜዳ የገቡት ። ያም ወደ ውጤት ተቀይሮ ጨዋታው ሦስት እኩል ተጠናቋል ። በደርሶ መልስ የ5 ለ4 ውጤት የጀርመን ቡድን ወደ ግማሽ ፍጻሜ ማለፍ ችሏል ።

በመጀመሪያው አጋማሽ ጣሊያኖች ላይ ሁለተኛው ግብ የተቆጠረው በተጨዋቾቹ አሳፋሪ ድርጊት ነበር ። የ15 ዐመቱ ኳስ አቀባይ ኖኤል ዑርባኒያክ ለዮሹዋ ኪሚሽ የማእዘን ምቱን ቶሎ እንዲመታ በፍጥነት ኳስ በማቀበል ሁለተኛዋ ግብ እንድትቆጠር አስተዋፅኦ አድርጓል ።  ኳስ አቀባዩ ኳሷን ከማቀበሉ ጥቂት ቀደም ሲል የጀርመን ተከላካይ አንቶኒዮ ሩዲገር ያሻማትን ኳስ አጥቂው ቲም ክላይንዲንስት በጭንቅላት ገጭቶ ግብ ጠባቂው ጂያንሉጂ ዶማ ሩማ በድንቅ ሁኔታ አጨናግፎ ከግቡ ጀርባ ኳሷን ይልካል ። ከዚያም ጂያንሉጂ ዶማሩማ የማእዘን ምት መሰጠቱን ዘንግቶ እንዴት ኳሱን አስመታችሁ በሚል ከተከላካዮች ጋር ለመጨቃጨቅ የግብ ክልሉን ጥሎ ወደፊት ይሄዳል ።  ከኋላው ያሉትን ዮሹዋ ኪሚሽ እና ጃማል ሙሳይላን አላስተዋለም ።

የጀርመን ቡድን ንቃት

በዐይን እይታ ብቻ የተግባባው ኳስ አቀባዩ ቶሎ ኳሷን ለዮሹዋ ኪሚሽ ይወረውርለታል፥ ዮሹዋ ኪሚሽ ለጃማል፥ ግብ ጠባቂውም ተከላካዮችም ከጭቅጭቃቸው ሳይወጡ እና ሳይነቁ ጃማልም ኳሷን ከመረብ ያሳርፋል ። እን ዶማሩማ ዞር ሲሉ ግቡ ተቆጥሯል ። የጃማል ሙሳይላ፤ ዮሹዋ ኪሚሽ እና የኳስ አቀባዩ ኑኤል የጋራ ጥረት የታከለባት ግብ ልትባል ትችላለች ። ለቅፅበት ተዘናግተው ጭቅጭቅ ላይ ማተኮራቸው ጣሊያኖችን ጉድ አድርጓቸዋል ። የጀርመን ተጨዋቾች በተለይ ከረፍት በፊት በተገኘው አጋጣሚ የተሰጣቸውን ኃላፊነት በአግባቡ መወጣታቸውን ያስመሰከሩበት ግጥሚያ ነበር ። ዮሹዋ ኪሚሽ ከጣልያን ጋር በነበረው የደርሶ መልስ ግጥሚያ በተቆጠሩት እምስት ግቦች በአጠቃላይ ቀጥተኛ ተሳትፎ አድርጓል ። አንዷን በመልሱ ግጥሚያ ትናንት በፍፁም ቅጣት ምት አስቆጥሯል ።

የጀርመን የኋላ መስመር ተከላካይ አንቶኒዮ ሩዲገር አጥቂው ቲም ክላይንዲንስትን ዘሎ ሲያቅፈው
የጀርመን የኋላ መስመር ተከላካይ አንቶኒዮ ሩዲገር አጥቂው ቲም ክላይንዲንስትን ዘሎ ሲያቅፈው ። አንቶኒዮ ሩዲገር ድንቅ ብቃቱን ዐሳይቷል ምስል፦ Christof Koepsel/Getty Images

ከእረፍት መልስ፦ የጣሊያን ቡድን ወደ ማጥቃቱ አጨዋወቱን ቀይሮ ማስጨነቁም ተሳክቶለት ነበር ። የሌሮይ ሳኔ ስህተት ሰበቡም ይኸው አስጨንቆ የመጫወት ስልት ውጤት ነው ። ሌሮይ ሳኔ በቀኝ ክንፈ ጫና ሲበዛበት ኳሷን ባልተመጠነ ሁኔታ ወደ መሀል ለዮሹዋ ኪሚሽ ይልካል፥ ሆኖም ኳሷ የጣሊያን አጥቂ ሞይሴ ኪን እግር ላይ ታርፋለች ። ። በዚያም ሞይሴ ለጣሊያን አስቆጥሮ ቡድኑ ተስፋ እንዲሰንቅ አድርጓል ።  ሁለተኛውንም ይኸው ፀጉረ ጉዱሩው ሞይሴ ኪን አስቆጥሯል ።

ጀርመን ላይ ሁለተኛው ግብ ሲቆጠርም የመጨረሻው ተከላካይ ታህ ወደፊት ከመውጣት ይልቅ ወደኋላ እያፈገፈገ ለመከላከል መሞከሩ ግቡ እንዲቆጠር አድርጓል ። የማታ ማታ የጣሊያን ቡድን ሦስት እኩል ቢወጣም በደርሶ መልስ ግን ጀርመን ወደ ግማሽ ፍጻሜው አልፏል ። በሩብ ፍፃሜው የዶርትሙንዱ ኤዱና ፓርክ ስታዲየም በደጋፊዎች ደምቃ አምሽታለች ። ሽቱትጋርት እና ሙይንሽን የግማሽ ፍፃሜ ጨወታዎችን ያስተናግዳሉ ።

የጣሊያን ልፋት እና ሽንፈት

የጣሊያን አቻውን በሩብ ፍጻሜው ያሸነፈው የጀርመን ብሔራዊ የእግር ኳስ ቡድን ሙይንሽን እና ሽቱትጋርት ከተሞች ውስጥ በሚካሄዱ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ተሳታፊ ይሆናል ።  ሁለቱ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ለረቡዕ፤ ግንቦት 27 እና በነጋታው ቀጠሮ ተይዞላቸዋል ። የፍጻሜ ግጥሚያው እሁድ ሰኔ 1 ቀን፤ 2017 ዓ.ም ቱሪን ጣሊያን ውስጥ ይካሄዳል ። 

ትናንት በነበሩ የኤሽንስ ሊግ ግጥሚያዎች ፖርቹጋል ከዴንማርክ ጋር ተጫውታለች ። የ40 ዐመቱ ክርስቲያኖ ሮናልዶ የተገኘችውን ፍፁም ቅጣት ምት ለግብ ጠባቂው አስታቅፎታል ።  ሆኖም 38ኛው ደቂቃ ለይ ብሩኖ ፈርናንዴሽ በግራ በኩል ያሻማትን ኳስ ክርስቲያኖ በጭንቅላት ሊገጭ ሲዘል የዴንማርኩ ተከላካይ ዮአኺም አንደርሰን ኳሷን አጨናግፋለሁ ብሎ በገዛ መረቡ ላይ በጭንቅላት ገጭቶ አሳርፏል ። 72ኛው ደቃ ላይ ክርስቲያኖ ሮናልዶ ፖርቹጋል 2 ለ1 እንድትመራ ያደረገውን ግብ ከማእዘኑ በቀኝ በኩል ሰውነቱ አጠማዝዞ በድንቅ ሁኔታ አስቆጥሯል ። 76ኛ ደቂቃ ላይ ክርስቲያን ኤሪክሰን ዴንማርክን ሁለት እኩል ያደረገችውን ግብ አስቆጠረ ።

መደበኛ 90 ደቂቃው 3 ለ2 ቢጠናቀቅም በደርሶ ምልስ ውጤት ሦስት እኩል በመሆኑ ጨዋታው እንዲራዘም ደቂቃ ተጨምሯል ። በተራዘመው ጨዋታ ፖርቹጋል ዴንማርክን 5 ለ2 ድል አድርጋ ወደ ግማሽ ፍፃሜ አልፋለች ። በግማሽ ፍፃሜው ከጀርመን ጋር ትጋጠማለች ።

በአውሮጳ ኔሽንስ ሊግ የጀርመን እና ጣሊያን ግጥሚያ
በአውሮጳ ኔሽንስ ሊግ የጀርመን እና ጣሊያን ግጥሚያ፦ ጀርመን አሸንፋ ወደ ግማሽ ፍጻሜው አልፋለች። ጂያንሉጂ ዱማሩማ የዮሹዋ ኪሚሽን ፍጹም ቅጣት ምት ማጨናገፍ አልቻለም ምስል፦ Alex Grimm/Getty Images

ስፔን ከኔዘርላንድ በደርሶ መልስ ግጥሚያው 3:3 ተጠናቆ በመለያ ምት ስፔን ኔዘርላንድን 5 ለ4 በአጠቃላይ 8 ለ7 ድል አድርጓል ። የ16 ዐመቱ ላሚን ጃማል ለስፔን ሦስተኛዋን ወሳኝ ግብ አስቆጥሯል ። ፈረንሣይ ክሮሺያን በመልሱ ጨዋታ በኦሊሴ እና ዖስማን ዴምቤሌ ግቦች 2 ለ0 ብታሸንፍም በደርሶ መልስ 2 ለ2 በመጠናቀቁ ጨዋታው እንዲራዘም ተደርጓል ። በተራዘመው ጨዋታ አሸናፊውን መለየት ባለመቻሉም በመለያ ምት ፈረንሣይ ክሮሺያን 5 ለ4 አሸንፋለች ። የመጋቢት 01 ቀን፣ 2017 ዓ.ም የስፖርት ዘገባ

የፎርሙላ አንድ

በሻንጋይ የቻይና ግራንድ ፕሪ የፎርሙላ አንድ ሽቅድምድም፦ የማክለረን አሽከርካሪዎች አንደኛ እና ሁለተኛ ወጡ ።  በትናንቱ ሽቅድምድም ዖስካር ፒያስትሪ አንደኛ በመውጣት 25 ነጥብ ሲያገኝ፤ የቡድን አጋሩ ላንዶ ኖሪስ ሁለተኛ በመውጣት 18 ነጥብ አግኝቷል ።  የመርሴዲሱ ጆርጅ ሩሴል በትናንቱም ውድድር እንዳለፈው ሽቅድምድም ሦስተኛ ደረጃ አግኝቶ 15 ነጥብ አግኝቷል ። በ4ኛነት ያጠናቀቀው የሬድ ቡል አሽከርካሪው ማክስ ፈርሽታፐን 12 ነጥብ አግኝቷል ። ሌዊስ ሐሚልተን በፌራሪ ተሽከርካሪው ሳያጠናቅቅ በመቅረቱ የ19ኛ ደረጃ ይዟል ። 

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ፀሐይ ጫኔ

   

 

ማንተጋፍቶት ስለሺ ሥዩም Mantegaftot Sileshi ዜና አዘጋጅ፤ መርኃ ግብር መሪ፤ የሳምንታዊ ስፖርት አዘጋጅ ነው፥ በአጭር ፊልም የበርካታ ዓለም አቀፍ ተሸላሚው ማንተጋፍቶት የቪዲዮ ዘገባዎችንም ያዘጋጃል።@manti