1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

በዋግኸምራ ዞን አስተዳደር ከ4,000 በላይ አርሶ አደሮች በተፈጥሮ አደጋ መጎዳታቸው

ኢሳያስ ገላው
ማክሰኞ፣ ነሐሴ 27 2017

በአማራ ክልል በዋግኸምራ ዞን አስተዳደር ከ4,000 በላይ አርሶ አደሮች በተፈጥሮ አደጋ ተጎድተዋል። በጸግብጂ ወረዳ 4 ቀበሌዎች በረዶ፣ ንፋስ እና ከባድ ዝናብ የአርሶ አደሮችን እርሻ ሙሉ በሙሉ ወድሟል፣ የሰው ሕይወት ጠፍቷል፣ ቤቶች ወድመዋል፣ ንብረታቸውንም ወስዷል።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4zt4r
ከabድ ዝናብ ያስከተለው ጉዳት
በአማራ ክልል በዋግኸምራ ዞን አስተዳደር የወረደው በደሮና ከባድ ዝናብ የአርሶ አደሩን እርሻ እንዳልነበረ አድርጓል። ምስል፦ Seyoum Abate

ከ4,000 በላይ አርሶ አደሮች በተፈጥሮ አደጋ መጎዳታቸው

ተደጋጋሚ የተፈጥሮ አደጋ የሚከሰትበት በአማራ ክልል የዋግህምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን በ2017/18 የክረምት ወቅት በረዶና ንፋስ ቀላቅሎ በጣለ ዝናብ በብሔረሰብ ዞኑ ፃግብዥ ወረዳ 4 ቀበሌዎች የመኸር እርሻ ሙሉ በሙሉ መውደሙን የወረዳው ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቋል።  በወረዳው 06 ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ገብሬ ግዛው ከነሐሴ 1 ቀን ጀምሮ በጣለው ከባድ ዝናብ 1198 አርሶ አደር እርሻ በጎርፍ መወሰዱን እና ለቤት እንስሳት የሚሆን መኖ እንዳልቀረ ይናገራሉ። «በረዶና ጎርፍ በቀላቀለ ዝናብ የተከልነውን ሰብል ወስዷል፤ በጭራሽ የሚባላ የለም የ30 አባወራ ማሳ ነው የተረፈው። ለከብት መኖ የለም፤ የአርሶ አደሩ ብዛት 1198 ነው።» 

ምንም ዓይነት ምላሽ ያላገኘዉ የተፈጥሮ አደጋ

በጻግብዥ ወረዳ 08 ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ዘይኑን ካሱ በመኸር እርሻ ወቅት የተተከለ ማሽላ በቆሎም ሆነ ልዩ ልዩ ሰብሎች በሙሉ በጎርፍ መጥፋታቸውን ይናገራሉ።

573 አባወራ አርሶ አደር የተጎዱበት በጻግብዥ ወረዳ የ010 ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ብርሃኑ ይግዛው የዘራነው ዘር በሙሉ በበረዶ ወድሞብናል፤ ከመንግሥት ግን ምንም ዓይነት ድጋፍ ማግኘት አልቻልንም ይላሉ። «በእኛ ቀበሌ የደረሰው ችግር በረዶ ነው የወደቀብን 573 አባወራ ተጎድቷል። ያው ለመንግሥት ግብርና ባለሙያ ሪፖርት ተደርጎ ነበር ምላሽ አልተገኘም።»

በአማራ ክልል በዋግኸምራ ዞን አስተዳደር የተፈጥሮ አደጋ
በአማራ ክልል በዋግኸምራ ዞን አስተዳደር ከ4,000 በላይ አርሶ አደሮች በተፈጥሮ አደጋ ተጎድተዋል። በጸግብጂ ወረዳ 4 ቀበሌዎች በረዶ፣ ንፋስ እና ከባድ ዝናብ የአርሶ አደሮችን እርሻ ሙሉ በሙሉ ወድሟል፣ የሰው ሕይወት ጠፍቷል፣ ቤቶች ወድመዋል፣ ንብረታቸውንም ወስዷል። ምስል፦ Seyoum Abate

ወረዳው ከሰሜኑ ጦርነት ጀምሮ ተደጋጋሚ ጉዳት አስተናግዶል

በጻግብዥ ወረዳ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ ሥዩም አባተ በሰሜኑ ጦርነት ከፍተኛጉዳት ያስተናገደው እና በመልሶ ማቋቋሙ ምንም ዓይነት ትኩረት ያልተሰጠው ጻግብዥ ወረዳ ከባለፈው ዓመት ጀምሮ መደበኛ ባልሆነ ዝናብ ጉዳት እየደረሰበት መሆኑን ገልጸዋል። 

በአደጋው የአንድ ሰው ሕይወት ሲጠፋ 19 ቤቶች ሙሉበሙሉ ወድመዋል። 4585 የማኅበረሰብ ክፍልም ለችግር ተዳርጓል የሚሉት አቶ ሥዩም አባተ ለመንግሥት የደረሰውን አደጋ ብናሳውቅም ምላሽ ማግኘት አልተቻለም ይላሉ።

«ባድሊባኖስ፣ ሰላምጌ፣ እምሊ አልበሳ፣ ፀፀጥነው፣ ቂርቆስ የሚባሉ ቀበሌዎችን ነው በረዶ የመታው 19 ቤቶች ፈርሰዋል አንድ ሰው ሞቷል እንስሳትም ጉዳት ደርሶባቸዋል። ለእነኝህም ምንም ድጋፍ አልተደረገም።»

የዋግ ህምራ ብሔረሰብ ዞን የጉዳቱን መጠን አላሳወቀም 

የዋግህምራ ብሔረሰብ ዞን አስተዳደር አስተዳዳሪ አቶ ኃይሉ ግርማይ እና የግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አዲሱ ወልድዬ የተፈጠረውን አደጋ በተመለከተ ለማናገር ብንደውልም ስልካቸው አይሠራም። ይሁን እንጂ የአማራ ክልል አደጋ መከላከል እና ምግብ ዋስትና  ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሰርክአዲስ አታሌ በዋግህምራ ብሔረሰብ ዞን ጉዳቱ ተለይቶ አልቀረበልንም ይላሉ፤ ተለይቶ ሲቀርብ ግን አስፈላጊውን ድጋፍ እናደርጋለን ብለዋል።

ኢሳያስ ገላው

ሸዋዬ ለገሠ

እሸቴ በቀለ