በጋዛ ከ40 በላይ ፍልስጤማውያን በእስራኤል የአየር ጥቃቶች ተገደሉ
እሑድ፣ ሐምሌ 6 2017በጋዛ ሕጻናትን ጨምሮ ውኃ ለመቅዳት በመጠባበቅ ላይ የነበሩ 10 ፍልስጤማያውን በተፈናቃዮች መጠለያ ውስጥ በእስራኤል የአየር ጥቃት መገደላቸውን የግዛቲቱ የሲቪል ሰዎች ደህንነት ጥበቃ ኤጀንሲ አስታወቀ። ድርጅቱ ለሊቱንና ዛሬ ማለዳ ብቻ ከ40 በላይ ፍልስጤማውያን በእስራኤል የአየር ጥቃት መገደላቸውን እንደገለጸ የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል።
የእስራኤል እና የሐማስ ልዑካን ለ 21 ወራት የዘለቀውን አሰቃቂ ውጊያ የሚያቆም ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ላይ ለመስማማት ሲደራደሩ አንድ ሣምንት አሳልፈዋል። ይሁንና በቃጣር ዋና ከተማ ዶሐ በመካሔድ ላይ በሚገኘው ቀጥተኛ ያልሆነ ድርድር ከሥምምነት ላይ እንዳይደረስ በማሰናከል ትላንት ቅዳሜ አንዳቸው ሌላቸውን ከሰዋል።
ሁለቱ ወገኖች በተዘዋዋሪ ሲደራደሩ ግን እስራኤል በጋዛ የምትፈጽመውን ጥቃት እንደቀጠለች ነው። በሰሜናዊ ጋዛ ከተማ በሚገኙ መኖሪያ ቤቶች ላይ በተፈጸሙ ጥቃቶች ስምንት ሰዎች መገደላቸውን የሲቪል ሰዎች ደህንነት ጥበቃ ኤጀንሲ ቃል አቀባይ ማሕሙድ ባሳል ተናግረዋል።
በማዕከላዊ ጋዛ በሚገኘው ኑሴይራት የተፈናቃዮች መጠለያ ጣቢያ ላይ በተፈጸመ ጥቃት 10 ሰዎች መገደላቸውን ቃል አቀባዩ ገልጸዋል። በዚያው በኑሴይራት የተፈናቃዮች መጠለያ የመጠጥ ውኃ ማከፋፈያ ቦታ ላይ በተፈጸመ ጥቃት ስምንት ሕጻናትን ጨምሮ 10 ሰዎች መገደላቸውን ማሕሙድ ባሳል መናገራቸውን የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ዘግቧል።
ሌሎች 11 ፍልስጤማውያን ደግሞ በጋዛ ከተማ የሚገኝ ገበያ ላይ በተፈጸመ ጥቃት ሕይወታቸውን አጥተዋል።
የጋዛ የሲቪል ሰዎች ደህንነት ጥበቃ ኤጀንሲ ቃል አቀባይ ማሕሙድ ባሳል እንዳሉት በአጠቃላይ 43 ሰዎች በእስራኤል የለሊት እና የዛሬ ማለዳ ጥቃቶች ተገድለዋል።
በሐማስ የሚመራው የጋዛ የጤና ሚኒስቴር ውጊያ ከተጀመረ ወዲህ 58,026 ፍልስጤማውያን መገደላቸውን አስታውቋል።