1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

በአማራ ክልል ሆስፒታሎች የኢትዮጵያ የጤና ባለሙያዎችን ጥያቄዎች የደገፉ ሰልፎች ተካሔዱ

ዓለምነው መኮንን
ቅዳሜ፣ ግንቦት 2 2017

የጤና ባለሙያዎችን የማህበራዊ ንቅናቄ ዘመቻ በመደገፍ በአማራ ክልል የተለያዩ የጤና ተቋማት ሠላማዊ ሰልፎች ተካሂደዋል፡፡ ባለሙያዎቹ ጥያቄዎቻቸው ምላሽ ካላገኙ ከነገ ጀምሮ የሥራ ማቆም አድማ እንደሚያደርጉ ከአንድ ወር በፊት አስጠንቅቀዋል። የጤና ሚኒስቴር ለባለሙያዎች ጥያቄዎች እውቅና እንድሚሰጥና በእቅድ ምላሸ እንደሚሰጥ ቀደም ሲል አሳውቋል፡፡

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4uD0u
የደብረታቦር ሆስፒታል
በአማራ ክልል ዛሬ ሰልፍ ካካሄዱ ተቋማት መካክል የደብረታቦር ሆስፒታል አንዱ ሲሆን የሰልፉን ዓላማ በተመለከተ የአንድ፣ “ሠልፉ በግቢ ውስጥ ተካሂዷል፣ በዋናነት ሰልፉ ለአገር አቀፉ የጤና ባሙያዎች ንቅናቄ ድጋፍ መስጠት ነው “ ብለዋል፡፡ምስል፦ Alemnew Mekonnen/DW

በአማራ ክልል ሆስፒታሎች የኢትዮጵያ የጤና ባለሙያዎችን ጥያቄዎች የደገፉ ሰልፎች ተካሔዱ

በአገር አቀፍ ደረጃ የጤና ባልሙያዎች ከደመወዝና ሌሎች ጥቅማጥቅም ክፍያዎች አለመመጣጠን ጋር በተያያዘ የማህበራዊ ንቅናቄ ዘመቻዎችን ካደረጉ አንድ ወር እየሞላቸው ነው፡፡ 12 ጥያቄዎቻቸውንም እንዲመለሱላቸው ለጤና ሚኒስቴር ማስገባታቸውን ንቅናቄውን የሚመሩ ባለሙያዎች ይገልፃሉ፡፡

በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ የጤና ባለሙያዎች ንቅናቄውን በመደገፍ ሰላማዊ ሰልፎችን እያካሄዱ ነው፡፡ በአማራ ክልል ዛሬ ሰልፍ ካካሄዱ ተቋማት መካክል የደብረታቦር ሆስፒታል አንዱ ሲሆን የሰልፉን ዓላማ በተመለከተ የአንድ፣ “ሠልፉ በግቢ ውስጥ ተካሂዷል፣ በዋናነት ሰልፉ ለአገር አቀፉ የጤና ባሙያዎች ንቅናቄ ድጋፍ መስጠት ነው “ ብለዋል፡፡

በደብረማርቆስ ሆስፒታል ገቢ ውስጥ  በተመሳሳይ ባልሙያዎቹ ሠልፍ ያካሄዱ ሲሆን ባልሙያዎቹ በሰልፋቸው “እየራበን አንሰራም፣ ተገቢው ክፍያ ይከፈለን” የሚሉና ሌሎች መልዕክቶች ተላልፈዋል ነው ያሉት፡፡

በህክምና ሙያ ተመርቃ ተሰዳ ለመስራት የተገደደች ወጣት

በባሕር ዳር ጥበበ ጊዮን ሆስፒታል በተደረግው የጤና ባለሙያዎች ሠልፍ፣ የትርፍ ሰዓት ክፍያ እስከ 4 ወራት እንደማይከፈላቸው ተግልጧል፣ ለአግራዊ የጤና ባለሙያዎች ያላቸውን አጋርነትም የገለፁበት ሠልፍ እንደነበረም አንድ አስተያየት ሰጪ አመልክተዋል፡፡

ፈለገ ሕይወት አጠቃላይ ሆስፒታል
“እንደሀገር የተነሳው የጤና ባለሙያዎች ጥያቄ እኛንም ይመለከታል” ያሉ የጤና ባለሙያዎች በፈለገ ሕይወት አጠቃላይ ሆስፒታል ግቢ ሠላማዊ ሰልፍ አድርገዋል። ምስል፦ DW

ትናንት በፈለገ ሕይወት አጠቃላይ ሆስፒታል ግቢ የተደርገውን ሠላማዊ ሰልፍ በማስመልከት ደግሞ አንድ የህክምና ባለሙያን ጠይቀን የሚከተለውን ምላሽ ስጥተዋል፡፡

“እኛም እንደሀገር የተነሳው የጤና ባለሙያዎች ጥያቄ እኛንም ይመለከታል በሚል መሰረታዊ ጥያቄ የጠየቅን መሆኑን፣ የመኖር አለመኖር ጥያቄ የጠየቅን መሆኑና እኛም እንደሀገር ለመጣው የጤና ባለሙያው ንቅናቄ አካል መሆናችንን በይፋ ለመግለፅ ነው” ብለዋል፡፡

በአማራ ክልል የሚደረገዉ ግጭት በጤና ባለሙያዎች ስራ ላይ ያደረሰዉ ጫና

የጎንደር ሆስፒታል ሠራተኞች በተመሳሳይ ንቅናቄውን በመደገፍ ሠላማዊ ሰልፍ ሰሞኑን ያካሄዱ ሲሆን የሆስፒታሉና የከተማዋ ጤና መምሪያ ኃላፊዎች በጉዳዩ ዙሪያ ከሰራተናወ ጋር ውይይት ቢያደርጉም ንቅናቄው አገር አቀፍ መሆኑን ባልሙያዎቹ ለባለስልጣናቱ ማስረዳታቸውን አንድ ባልሙያ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል፡፡

የጤና ሚኒስቴር የጤና ኮሙዩኒኬሽንና የህዝብ ግንኙነት ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ተገኔ ረጋሳ ሰሞኑን እንደገለፁልን ለባልሙያው ጥያቄዎች እውቅና እንደሚሰጡና የጤና ባልሙያዎቹ ለሚያነሷቸው ጥያቄዎች በአጭር፣ በመካከለኛና በረጅም ጊዜ ለመፍታት እየተሰራ እንደሆነ አመልክተዋል፡፡

የጤና ባልሙያዎች ጥያቄዎቻቸው እንዲመለሱላቸው ከሚያዝያ 3/2017 ዓ ም ጀምሮ ለአንድ ወር የሚቆይ የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ንቅናቄ የጀመሩ ሲሆን ጥያቄዎቻቸው በተጥቀሰው የአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ምላሽ ካላገኙ የሥራ ማቆም አድማ እንደሚያደርጉ ማስጠንቀቃቸው ይታወሳል፣ የጤና ባለሙያዎች የሰጡት “የሥራ እናቆማለን” የማስጠንቀቂያ የጊዜ ገደብ ነገ ይጠናቀቃል፡፡

ዓለምነው መኮንን
እሸቴ በቀለ