በ2023 ዓ/ም በብዛት የተጫኑ መተግበሪያዎች የትኞቹ ናቸው?
ረቡዕ፣ ታኅሣሥ 24 2016
የጎርጎሪያኑን ዓዲስ ዓመት 2024ን ከተቀበልን ሶስተኛ ቀን ተቆጥሯል።ለመሆኑ በተሸኘው የጎርጎሪያኑ 2023 ዓ/ም በብዛት የተጫኑ መተግበሪያዎች የትኞቹ ናቸው? በ2024 በተጠቃሚዎች ተፈላጊ የሚሆኑትስ ? የዛሬው የሳይንስ እና ቴክኖሎጅ ዝግጅት ትኩረት ነው።
መረጃዎች እንደሚያሳዩት በዓለም አቀፍ ደረጃ ከ2.7 ቢሊዮን በላይ የስማርት ስልክ ተጠቃሚዎች አሉ። 1.14 ቢሊዮን ሰዎችም ታብሌት ይጠቀማሉ። ይህ ቁጥርም ባለፉት ስድስት ዓመታት ወደ 36 በመቶ ገደማ ማደጉ ይነገራል።
እነዚህ ተንቀሳቃሽ ዲጅታል መሳሪያዎች ከሰዎች ጋር ያላቸው ትስስርም ከፍተኛ ነው። በስራ ቦታ፣ቤት ውስጥ ፣መንገድ ላይ፣እና በመኪና ውስጥ ሳይቀር ለተለያዩ አገልግሎቶች እንጠቀማለን። ምናልባትም ይህንን ፕሮግራም በተንቀሳቃሽ ስልክ እያደመጡ እያነበቡ ሊሆን ይችላል።
ጥናቶች እንደሚያሳዩት አሜሪካውያን በአማካይ በቀን 262 ጊዜ ስልካቸውን ይፈትሻሉ። ይህም በየ 5.5 ደቂቃዎች አንድ ጊዜ እንደ ማለት ነው።
በሌላ በኩል የተንቀሳቃሽ ስልክ መተግበሪያዎች መረጃ ለማግኘት ፣ለግብይት፣ለመጓጓዣ አገልግሎት፣የአየር ትንበያን ለመከታተል እና ለሌሎች አገልግሎቶች ውጤታማ እየሆኑ በመምጣታቸው፤ ተጠቃሚዎች በተንቀሳቃሽ ስልኮች ከሚያጠፉት ጊዜ ውስጥ 90 በመቶ በላይ የሚሆነውን መተግበሪያዎች ላይ ያውሉታል።
ከዚህ አኳያ የተንቀሳቃሽ ስልክ መተግበሪያዎችን አውርደው የሚጠቀሙ ሰዎች ቁጥርም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል።
በተራኪ መተግበሪያ በሚተላለፈው ጉጉት ፖድካስት አዘጋጅ እና የሶፍትዌር ምህንድስና ባለሙያ የሆነው ወጣት ብሩክ በልሁ እንደሚለው ይህ አዝማሚያ የሚጠበቅ ነው።
በዓለም አቀፍ ደረጃ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች መረጃዎችን የሚተነትነው ስታስቲታ የተባለው መድረክ ባወጣው መረጃ መሠረት፤ የተንቀሳቃሽ ስልክ መተግበሪያ አጠቃቀም በዓለም ዙሪያ እያደገ ሲሆን፤ከጥቂት ቀናት በፊት በተጠናቀቀው የጎርጎሪያኑ 2023 ዓ/ምም መተግበሪያዎችን የሚያወርዱ ሰዎች ቁጥር ጨምሯል። ይህ አዝማሚያ በሚቀጥሉት ዓመታትም ይቀጥላል።
በዚህ መሰረት በተሸኘው የጎርጎሪያኑ 2023 ዓ/ም ከአንድሮይድ ጎግል ፕሌይ እና ከአፕል iOS በብዛት የተጫኑ መተግበሪያዎችን ስንመለከትም፤ዋትስአፕ የመጀመሪያ ደረጃ ሲይዝ ፌስቡክ ሜሴንጄር እና የቻይናው ባይትዳንስ ኩባንያ ይፋ ያደረገው ቲክቶክ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ።
ፌስቡክ፣ኢንስታግራም፣ሸርኢት፣ዩቱዩብ፣ በቅደም ተከተል ከአራት እስከ ሰባት ያለውን ቦታ ይይዛሉ።ላይክ ቪዲዮ፣ ኔትፍሊክስ እና ስናፕቻት ደግሞ ከስምንት እስከ አስር ያለውን ደረጃ ይዘዋል።
ከላይ የተዘረዘሩት መተግበሪያዎች ከጎግል ፕሌይ እና ከአፕ ስቶር ከሁለቱም በተሰበሰበ መረጃ ቢሆንም፤በጎርጎሪያኑ ሰኔ 2023 ዓ/ም በተሰበሰበ መረጃ ኢንስታግራም በዓለም ዙሪያ ሰዎች ከአንሮይዱ ከጎግል ፕሌይ/Google Play/ በብዛት አውርደው የተጠቀሙበት መተግበሪያ እንደነበር ስታስቲታ አስፍሯል።
የአንሮይድ ጎግል ፕሌይ መተግበሪዎች ከአፕሉ iOS ጋር ሲነፃጸርም፤ የአንሮይድን መተግበሪያዎች አውርደው የሚጠቀሙ ሰዎች ቁጥር ብልጫ እንዳለው መረጃው አመልክቷል።
በነፃ የሚጫኑ መተግበሪያዎች ደግሞ ከሚከፈልባቸው መተግበሪያዎች የበለጠ ተጠቃሚ እንዳላቸው ተመልክቷል።
ነገር ግን እነዚህን የማይከፈላቸውን መተግበሪያዎች በሚጭኑበት ወቅት ተጠቃሚዎች የግል መረጃዎቻቸው ለጥቃት እንዳይጋለጡ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለባቸው ባለሙያው ይመክራል።የስማርት ስልኮቻችንን ደህንነት እንዴት እንጠብቅ?
እንደ ስናፕ ቻት /Snapchat/፣ ፌስቡክ/Facebook/ እና ሜሴንጀር እንዲሁም ኢንስታግራም/Instagram/ ያሉ የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች መተግበሪያዎች በሁለቱም ማለትም በአንሮይድ እና በአይ ኦ ኤስ ስርዓቶች በብዛት ከተጫኑ 10 ዝርዝር ውስጥ ተካተዋል። ይህም ተጠቃሚዎች አሁንም በእጃቸው ባለው ቴክኖሎጅ ፈጣን ግንኙነት እንደሚፈልጉ ይጠቁማል።
እንደ ዎርድስትሪም ዘገባ የሜታ ንብረት የሆኑት ኢንስታግራም፣ ፌስቡክ እና ዋትስአፕ በድምሩ ከ1 ነጥብ 4 ቢሊየን በላይ ሰዎች ጭነውቸዋል።በተለይ ፌስቡክ 75 በመቶ የሚሆኑት ወንድ የበይነመረብ ተጠቃሚዎች እና 83 በመቶ የሚሆኑ ሴት የበይነመረብ ተጠቃሚዎች ንቁ ተጠቃሚዎቹ ናቸው።
የቻይናው ባይትዳንስ ኩባንያ ንብረት የሆነው ቲክቶክም በተጠናቀቀው ዓመት በርካታ ደንበኞችን ያፈራ ሲሆን፤ በ2023 የመጀመሪያ አጋማሽ ብቻ 672 ሚሊየን ሰዎች አውርደው ተጠቅመውበታል።ጠቅላላ ተጠቃሚዎቹ ደግሞ በ2023 ዓ/ም 1 ነጥብ 5 ቢሊየን ደርሰውለታል።
በአጠቃላይ በተሸኜው 2023 ዓ/ም በብዛት ከተጫኑ አስር መተግበሪያዎች ውስጥ ቀደም ሲል ታዋቂ የነበሩ የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ሰዎች በብዛት የጫኗቸው መተግበሪያዎች በመሆን አሁንም ድረስ ተቀባይነታቸው ጉልህ መሆኑን አሳይተዋል።ለዚህም ብሩክ በርካታ ምክንያቶችን ያነሳል።
የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች መረጃዎችን በማድረስ እና የይዘት ፈጣሪዎችን ገቢ በማሳደግ ረገድ ጠቃሚ ቢሆኑም፤ከተጠቃሚዎች አኳያ ግን ሰዎች ለሌላ ምርታማ ስራ የሚያውሉትን ጊዜ መሻማት እና ትኩረት መስረቅ ከማህበራዊ መገናኛ ብዙሃን አጠቃቀም ጋር አብረው የሚመጡ ችግሮች ናቸው።
ከዚህ በተጨማሪ በመረጃ አያያዝ ደህንነት እና በይዘት ቁጥጥር ላይም ተደጋጋሚ ወቀሳ እና ክስ ሲቀርብባቸው ይታያል። ከዚህ አኳያ እንደ ፌስቡክ እና ቲክቶክ ያሉ የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ስለተቀመራቸውን /Algorithm/ሊያሻሽሉ እና ጠንካራ የይዘት ቁጥጥር ሊኖራቸው እንደሚገባ ባለሙያዎች ያሳስባሉ።ብሩክ ግን ተጠቃሚዎችም ሀላፊነት አለባቸው ይላል።
በሌላ በኩል ከዜና ይልቅ የመዝናኛ እንቅስቃሴን የሚያሳየው የዩቲዩብ፣ ኔትፍሊክስ እና 11 ኛ ደረጃን የያዘው ስፖቲፋይ/Spotify/ በ2023 ዓ/ም ተወዳጅነታቸው እየጨመረ መምጣቱን ዘገባው አመልክቷል።
ለምሳሌ፣ ዩቲዩብ ለተጠቃሚዎች ቅንጭብጫቢ መረጃዎችን የሚያደርስ ተደርጎ የተሰራ ቢሆንም፤ በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ከሚገኙ የኬብል ኔትወርክ ማሰራጫ ጣቢያዎች ይልቅ ዩቱዩብ ከ18-49 አመት እድሜ ያላቸውን ሰዎችን የበለጠ ይስባል።
ሰውሰራሽ አስተውሎትን የሚጠቀሙ እንደ ቻትጂፒቲ ያሉ መተግበሪያዎችም በተጠናቀቀው 2023 ዓ/ም በስፋት አገልግሎት ላይ ውለዋል።
በአጠቃላይ የተንቀሳቃሽ ስልክ መተግበሪያዎች የዕለት ተዕለት ሕይወታችን አካል መሆናቸው እየጨመረ በመምጣቱ፤ አዲሱ ዓመት 2024ም ለሞባይል መተግበሪያ ኢንዱስትሪ ትልቅ አመት ሆኖ ይቀጥላል።የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጅ ዕድል እና ፈተና
በዚህ ሁኔታ የተንቀሳቃሽ ስልክ መተግበሪያዎች አጠቃቀም ከፍተኛ እየሆነ መምጣቱ ደግሞ፤መተግበሪያ ላበለፀጉ እና ወይም ለማበልፀግ ላቀዱ ሁሉ አበረታች ነው ተብሏል።
ያም ሆኖ አዲስ የተንቀሳቃሽ ስልክ መተግበሪያ መስራት የሚፈልጉ የፈጠራ ባለሙያዎች ከላይ ከተጠቀሱት የማህበራዊ መገናኛ ዘዴ መተግበሪያዎች ውስጥ አንዱን የሚወዳደር እንዲሰሩ አይመከረም። «ያ ሰዎች ምግብ ስለሚወዱ ምግብ ቤት ልክፈት እንደማለት ነው።»ይላል ቢዩልድ ፋየር የተባለው መድረክ ያወጣው ዘገባ።
ያም ሆኖ ወደ ዋክብት መተኮስ ምንም ስህተት አይደለም። ነገር ግን መተግበሪያውን ውጤታማ ለማድረግ ፉክክሩ አቀበት የመውጣት ወይም የጦርነት ያህል ሊከብድ ይችላል።በማለት ቢዩልድ ፋየር ለፈጠራ ባለሙያዎች ምክር እና ሀሳብ ለግሷል።
ሙሉ ዝግጅቱን የድምፅ ማዕቀፉን ተጭነው ያድምጡ።
ፀሀይ ጫኔ
ዩሀንስ ገብረእግዚአብሄር