ሠልፍ በሀዋሳ
ቅዳሜ፣ ሐምሌ 22 2015ማስታወቂያ
በሀዋሳ ከተማ እምብርት ላይ የሚገኘው የሚሊኒም አደባባይ በተለምዶ ለፖለቲካ ሀይሎች የሚደረጉ የድጋፍ ወይም የተቃውሞ ሠልፎችን በማስተናገድ ነው የሚታወቀው ፡፡ አርብ ጠዋት በዚሁ አደባባይ የተሰባሰቡ የሲዳማ ክልል የመንግሥት ሠራተኞች ግን የክልሉን ነዋሪዎች ይቅርታ የሚጠይቅ ሰልፍ አካሂደውበታል ፡፡
ከክልሉ የተለያዩ ቢሮዎችና ከሀዋሳ ከተማ አስተዳደር በመነሳት በአደባባዩ የተሰባሰቡት ሠልፈኞች ቁጥራቸው በሺህዎች ይገመታል ፡፡ የተለያዩ መፈክሮችን በመያዝ በሥፍራው ከተገኙት ሠልፈኞች መካከል ሦስቱ ለዶቼ ቬለ DW በሰጡት አስተያየት ወደ አደባባይ የመጡት እስከአሁን ይሰጡት በነበረው ደካማ አገልግሎት የተነሳ ቅር የተሰኙ ነዋሪዎችን ይቅርታ ለመጠየቅንና በቀጣይ በመልካም ሁኔታ ለማስተናገድ ቃል ለመግባት ነው ብለዋል ፡፡
ሲዳማ ክልል ሆኖ ከተዋቀረ ወዲህ ለህዝቡ መስጠት የሚገባውን ያህል አገልግሎት እንዳልሰጡም ሠልፈኞቹ በተወካያቸው አማካኝነት በንባብ ባሰሙት መግለጫ ጠቅሰዋል ፡፡በቀጣይ መደበኛ የሥራ ሰዓትን በማክበር ፣ የመንግሥትና የህዝብ ሀብትን በቁጠባ በመጠቀም እንዲሁም ከሙስናና ከአድሎ የፀዳ አገልግሎት በመስጠት ነዋሪውን ለማርካት እንደሚሠሩም ሠልፈኞቹ በአቋም መግለጫቸው ቃል ገብተዋል፡፡
ሸዋንግዛው ወጋየሁ