1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

መሐመድ ሐምዳን ደጋሎ የሱዳን ትይዩ መንግሥት መሪ ሆነው ቃለ-መሐላ ፈጸሙ

እሑድ፣ ነሐሴ 25 2017

መሐመድ ሐምዳን ደጋሎ የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል ከተወሰኑ ታጣቂ ቡድኖች ጋር የመሠረተው ትይዩ መንግሥት መሪ ሆነው ቃለ-መሐላ ፈጸሙ። የሱዳን ሕዝቦች ነጻ አውጪ ንቅናቄ አንድ አንጃ የሚመሩት አብደል አዚዝ አል-ሒሉ የመሐመድ ሐምዳን ደጋሎ ምክትል ሆነዋል። መቀመጫውን በኒያላ ከተማ ያደረገው ትይዩ መንግሥት ሱዳንን እንዳይሰነጥቃት አስግቷል።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4zlZw
የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል አዛዥ መሐመድ ሐምዳን ደጋሎ
ሔሜቲ በሚል ቅጽል ሥማቸው የሚታወቁት ደጋሎ 15 አባላት ያሉትን ፕሬዝዳንታዊ ምክር ቤት ለመምራት ቃለ-መሐላ የፈጸሙት ትላንት ቅዳሜ እንደሆነ ተመሠረተ የተባለው ትይዩ መንግሥት አስታውቋል። ምስል፦ Russian Foreign Ministry Press Service/TASS/IMAGO

መሐመድ ሐምዳን ደጋሎ የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል ከተወሰኑ ታጣቂ ቡድኖች ጋር የመሠረተው ትይዩ መንግሥት መሪ ሆነው ቃለ-መሐላ ፈጸሙ። ሔሜቲ በሚል ቅጽል ሥማቸው የሚታወቁት ደጋሎ 15 አባላት ያሉትን ፕሬዝዳንታዊ ምክር ቤት ለመምራት ቃለ-መሐላ የፈጸሙት ትላንት ቅዳሜ እንደሆነ ተመሠረተ የተባለው ትይዩ መንግሥት አስታውቋል። 

የሱዳን ሕዝቦች ነጻ አውጪ ንቅናቄን አንድ አንጃ የሚመሩት አብደል አዚዝ አል-ሒሉ የመሐመድ ሐምዳን ደጋሎ ምክትል ሆነዋል። የቀድሞዉ የሱዳን ሉዓላዊ ምክር ቤት አባል መሐመድ ሐሰን አል-ታይሺን ተመሠረተ የተባለው መንግሥት ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ተሾመዋል።

ደጋሎ የሚመሩት ፕሬዝዳንታዊ ምክር ቤት ሌሎች 13 አባላት ቃለ-መሐላ መፈጸማቸውን ትይዩው መንግሥት ያሠራጨው መግለጫ ይጠቁማል። የምክር ቤቱ አባላት ነባር እና ትይዩው መንግሥት የመሠረታቸው አዳዲስ ግዛቶችን እንዲያስተዳድሩ የተሾሙ አገረ ገዥዎች ናቸው። 

የቀድሞው ፕሬዚዳንት ኦማር አል በሽር ከሥልጣን ከተወገዱ በኋላ የተመሠረተውን ሉዓላዊ ምክር ቤት በሊቀ-መንበርነት እና ምክትል ሊቀ-መንበርነት ይመሩ በነበሩት መሐመድ ሐምዳን ደጋሎ እና የብሔራዊ ጦሩ አዛዥ አብደል ፋታኅ አል-ቡርኻን መካከል የተፈጠረው ልዩነት ሱዳንን ለብርቱ ጦርነት ዳርጓታል። ደጋሎ የተወሰኑ ታጣቂዎችን በማስተባበር የመሠረቱት መንግሥት ሀገሪቱን ለሁለት እንዳይሰነጥቃት ያሰጋ ነው። 

የሱዳን ሉዓላዊ የሽግግር ምክር ቤት ፕሬዝደንት ጀኔራል አብደል ፋታኅ አል-ቡርኻን ባለፈው ሰኔ ካሚል ኢድሪስን የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር አድርገው ሲሾሙ
የሱዳን ሉዓላዊ የሽግግር ምክር ቤት ፕሬዝደንት ጀኔራል አብደል ፋታኅ አል-ቡርኻን ባለፈው ሰኔ ካሚል ኢድሪስን የሱዳን ጠቅላይ ሚኒስትር አድርገው ሾመዋል። ምስል፦ Sudan Transitional Sovereignty Council/REUTERS

ደጋሎ “የሰላም እና የአንድነት መንግሥት” መመሥረታቸውን ያስታወቁት ባለፈው ሚያዝያ ወር ነበር። ይሁንና የአፍሪካ ኅብረት እና የአረብ ሊግ ለደጋሎ መንግሥት ዕውቅና እንደማይሰጡ አስታውቀዋል። ግብጽ እና ጅቡቲም ከዚህ ቀደም የደጋሎን ትይዩ መንግሥት ተቃውመው ነበር። 

የፈጥኖ ደራሽ ኃይል መሪ ሱዳንን ለሁለት እንዳይሰነጥቅ ያሰጋውን ትይዩ መንግሥት ለመምራት ቃለ-መሐላ የፈጸሙት በዳርፉር ግዛት በምትገኘው የኒያላ ከተማ ነው። በዳርፉር ግዛት ከሚገኙ ትልልቅ ከተሞች አንዷ የሆነችው ኒያላ የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል መቀመጫ ሆኖ እያገለገለች ትገኛለች። ከተማዋ ትላንት ቅዳሜ በድሮኖች ጥቃት እንደተፈጸመባት ሬውተርስ ዘግቧል። 

የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ኃይል አብዛኛውን የዳርፉር ግዛት የሚቆጣጠር ቢሆንም ታሪካዊቷን የኤል-ፋሽር ከተማ በእጁ ለማስገባት ከሱዳን ብሔራዊ ጦር እና አጋር ታጣቂዎቹ ጋር እየተፋለመ ይገኛል። የተወሰነው የኮርዶፋን ግዛት አነስተኛ የብሉ ናይል ግዛት በታጣቂ ቡድኑ ቁጥጥር ሥር ከሚገኙ መካከል ናቸው። 

መቀመጫውን በፖርት ሱዳን ያደረገው መንግሥት በአንጻሩ በምሥራቅ፣ በማዕከላዊ ሱዳን፣ በሰሜን እና በብሉ ናይል ግዛት የሚገኙ አካባቢዎችን ይቆጣጠራል። በሱዳን መደበኛ ጦር እና በፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ መካከል ከ28 ወራት ገደማ በፊት ውጊያ ከተቀሰቀሰ ወዲህ መሐመድ ሐምዳን ደጋሎ እምብዛም አይታዩም።

አርታዒ ታምራት ዲንሳ 
 

DW Mitarbeiterportrait | Eshete Bekele
Eshete Bekele Reporter specializing in topics directly related to Ethiopia and the Horn of Africa.@EsheteBekele