1. ወደ ይዘቱ እለፍ
  2. ወደ ዋናዉ ገጽ እለፍ
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ እለፍ

ወቅታዊ ሁኔታዎች ያዳከሙት የላሊበላ የቱሪዝም እንቅስቃሴ

ዓለምነው መኮንን
ሰኞ፣ ሰኔ 16 2017

በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ላሊበላ አካባቢ በነበሩ ሰው ሠራሽ ችግሮች ምክንያት ቅዱስ ላሊበላንና አካባቢውን ይጎበኙ የነበሩ ቱሪስቶች ቁጥር በመቀነሱ በዘርፉ ተሰማርተው የነበሩ አካላት ለከፍተኛ የኢኮኖሚ ችግር መዳረጋቸው ተመለከተ። በከተማዋ አገልግሎት ይሰጡ የነበሩ 52 ሆቴሎች የተሟላ አገልግሎት በማቆማቸው 5ሺህ ሰራተኞች ስራ አጥ ሆነዋል።

https://jump.nonsense.moe:443/https/p.dw.com/p/4wK5B
Ahesnday-Feier in der Region Amhara, Äthiiopien
ምስል፦ Alemnew Mekonnen/DW

ወቅታዊ ሁኔታዎች ያዳከሙት የላሊበላ የቱሪዝም እንቅስቃሴ

ወቅታዊ ሁኔታዎች ያዳከሙት የላሊበላ የቱሪዝም እንቅስቃሴ

በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ላሊበላ አካባቢ በነበሩ ሠው ሠራሽ ችግሮች ምክንያት ቅዱስ ላሊበላንና አካባቢውን ይጎበኙ የነበሩ ቱሪስቶች ቁጥር በመቀነሱ በዘርፉ ተሰማርተው የነብሩ አካላት ለከፍተኛ የኢኮኖሚ ችግር መዳረጋቸውን ተጠቃሚዎች ተናገሩ፣ በከተማዋ አገልግሎት ይሰጡ የነበሩ 52 ሆቴሎች የተሟላ አገልግሎት መስጠት በማቆማቸው 5ሺህ ሰራተኞች መበተናቸውን የቅዱስ ላሊበላ ሆቴሎች ማህበር አመልክቷል፣ የቅዱስ ላሊበላ ቱሪስት አስጎብኝ ድርጅት ማህበር በበኩሉ 200 አባላቱ በችግር ላይ መሆናቸውን አስታውቋል፡፡ግጭት ያቆረቆዘው ቱሪዝም

የቱሪስቱ ፍሰት በመዳከሙ ሆቴሎች ሥራ አቁመዋል” የላሊበላ ከተማ ነዋሪ

የላሊበላና አካባቢው ነዋሪዎች ዋና የገቢ ምንጫቸው ከቱሪዝም የሚገኝ ሀብት መሆኑን የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ፣ ወጣቶች በማህበር ተደራጅተው ያስጎበኛሉ፣ ሆቴሎች ለቱሪስቶች በሚሰጡት አገልግሎት ገቢ ያገኛሉ፣ ሌሎች ደግሞ የተለያዩ ባህላዊ ቁሳቁሶችን ለሀገር ውስጥና ለውጪ ቱሪስቶች በመሸጥ ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ያስተዳድራሉ፡፡ አንድ የከተማዋ ነዋሪ ለዶቼ ቬሌ እንደገለፁት፣ በመጀመሪያ ኮቪድ፣ በኋላም የሰሜኑ ጦርነት አሁን ደግሞ በክልሉ ያለው የሠላም እጦት ቱሪዝሙን በማዳከሙ በቱሪዝሙ ዘርፍ ያሉ ሁሉም የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች በእጅጉ ተጎድተዋል ነው ያሉት፡፡ “ሆቴሎች መቶ በመቶ በሚባል ደርጃ ሥራ አቁመዋል፣ ሥራ የለም” ሲሉ ተናግረዋል፡፡ወደ ትግራይ የሚጓዙ የዉጪ መንገደኞች የገጠማቸዉ ክልከላ

የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች ሳይቀር መምጣት አቁመዋል” የብልባላ ቀበሌ ነዋሪ

ከቱሪስት መስህቦች አንዱ በሆነው የሰሜን ወሎ ዞን ላስታ ወረዳ፣ የብልባላ ጊዮርጊስ ነዋሪ ቄስ ተስፋ አብቦ የአገር ውስጥ ጎብኝዎች ሳይቀር አሁን ባለው የፀጥታ ችግር ምክንያት ወደ አካባቢው እንደማይመጡ አመልክተው “የእደጥበብ ውጤቶችን የሚሸጡ ወጣቶችም ሥራ አቁመዋል” ነው ያሉት፡፡

የቅዱስ ላሊበላና አካባቢው ቱሪስት አስጎብኚ ማህበር ሰብሳቢ አቶ እስታሉ ቀለመወርቅ “ቱሪዝሙ አስጎብኝውን ብቻ ሳይሆን ከቱሪዝም ጋር በተያያዘ የሚሰሩ በርካታ የአካባቢውን ሠዎች ጎድቶታል” ብለዋል፡፡

እንደ አቶ እስታሉ፣ ቀደም ሲል በማህበር ተድራጅተው ያስጎበኙ የነበሩ 200 አባላት ያሉት የቱሪስት አስጎብኚ ማህበር የነበረ ቢሆንም ባሉ ችግሮች ምክን ያት የቱሪስቱ ፍስሰት በማሽቆልቆሉ፣ 30 የሚሆኑ አባላቱ አካባቢውን እንደለቀቁ ተናግረዋል፣ ቀሪዎቹም ቢሆኑ ያለሥራ መቀመጣቸውን አስረድተዋል፡፡

ፎቶ ከማኅደር፤ ላሊበላ
ፎቶ ከማኅደር፤ ላሊበላ ምስል፦ Michele Spatari/AFP/Getty Images

ሆቴሎች ሥራ በማቆማቸው 5ሺህ ሠራተኞች ተበትነዋል” የሆቴሎች ማህበር

በከተማዋ የመዘና ሪዞርትና ስፓ ባለቤትና የቅዱስ ላሊበላ ሆቴሎች ማህበር ሰብሳቢ አቶ ዮሐንስ አሰፋ ዋናው ገቢያቸው ቱሪዝም የነበሩ 52 ሆቴሎች አብዛኛዎች አገልግሎት በማቆማቸው 5ሺህ የሚሆኑ ሰራተኞቻቸ መበተናቸውን አስረድተዋል፡፡

በከተማዋ ያሉ ሆቴሎች ባለፉት 6 ዓመታት በዓመት አንድ ጊዜ የሚከበረውን የገና በዓል ምክንያት ከሚሰጡት አገልግሎት ውጪ ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ እንደሌለ ነው የገለጡት፡፡

መልሶ ወደ ሥራ ለመግባት ቢሞከር እንኳ የነበሩና ልምድ ያዳበሩ ሠራተኞችን ማግኝት ከባድ እንደሚሆን ነው ያመለከቱት፡፡ቱሪዝምና ሰላም በኢትዮጵያ፤ በቱሪዝም ሳምንት ሲወሳ

የቱሪዝሙን እንቅስቃሴ ለመመለስ እየተሰራ ነው” የላሊበላ ከተማ አስተዳደር

የላሊበላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ወንድምነው ወዳጄ ለዶይቼ ቬሌ እንደተናገሩት፣ የኮቪድ ስጋት፣ የሰሜኑ ጦርነትና አሁን ደግሞ በክሉሉ ያላው የፀጥታ ችግር ባለፉት 6 ዓመታት የቱሪዝሙን እንቀስቃሴ ጎድቶታል፡፡ ይሁን እንጂ የቱሪዝሙን እንቅስቃሴ ወደነበረበት ለመመልስ አስተዳደራቸው ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር እየሰራ እንደሆን ተናግረዋል፡፡

በላሊበላ ከተማና አካባቢው በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (UNESCO) የተመዘገቡ 11 የቅዱስ ላሊበላ አቢያተ ክርስቲያናትን ጨምሮ ሌሎች የቱርስት መስህቦች ይገኛሉ፡፡

ዓለምነው መኮንን

አዜብ ታደሰ

ዮሃንስ ገብረግዚአብሔር