ጀርመን እና ኢትዮጵያ የስምምነት ሰነድ ተፈራረሙ
ዓርብ፣ ነሐሴ 18 2010በጀርመን እና በኢትዮጵያ መንግስት መካከል ዛሬ የተደረገው ስምምነት የገንዘብ እና የቴክኒክ ድጋፍን ያካትታል። በጀርመን በኩል ስምምነቱን በፊርማቸው ያጸደቁት የሐገሪቱ የኢኮኖሚ ልማት እና ትብብር ሚኒስትር ጌርድ ሙለር ሲሆኑ በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ የገንዘብ እና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትሩ ዶ/ር አብርሃም ተከስተ ናቸው።
የጀርመን የኤኮኖሚ ልማት እና ትብብር ሚኒስቴር ዛሬ ባወጣው መግለጫ ኢትዮጵያን በመጎብኘት ላይ ያሉት ጌርድ ሙለር ሀገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ትብብርዋን እንደምታጠናክር ማስታወቃቸውን ገልጿል። ለኢትዮጵያ በጀርመን ሞዴል ለወጣቶች የሙያ ስልጠና ስርዓት እንደሚዘጋጅ እና ሀገሪቱ ለግል ባለሀብቶች የሰጠችውን አዲስ እድልም የሀገራቸው መንግሥት እንደሚጠቀምበት ሚኒስትሩ መግለጻቸውን ጠቁሟል። በኢትዮጵያ ረሀብን በመከላከል ረገድም ጀርመን ጠንካራ አጋር እንደምትሆንም ተጠቅሷል።
ስድስት መቶ ሺህ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች የሚገኙባትን ጋምቤላን የጎበኙት ሙለር በዚያ ለሚገኙ ስደተኞች የውሀ አቅርቦትን ለማሻሻል ጀርመን ተጨማሪ ድጋፍ እንደምታደርግ ተናግረዋል። ሙለር ከኢትዮጵያ ጉብኝታቸው በፊት በኤርትራ አስመራ ቆይታ አድርገው ነበር።
ጀርመን እና ኢትዮጵያ ዛሬ ያደረጉትን ስምምነት የተከታተለዉ የአዲስ አበባው ዘጋቢያችን ጌታቸው ተድላ ኃይለጊዮርጊስ ያጠናቀረውን ዘገባ የድምጽ ማዕቀፉን ተጭነው ያድምጡ።
ጌታቸው ተድላ ኃይለጊዮርጊስ
ተስፋለም ወልደየስ
ነጋሽ መሐመድ