የገዢው ብልጽግና ፓርቲ ጉባኤ እና የተደረገው ጥሪ
ሰኞ፣ ጥር 26 2017የገዢው ብልጽግና ፓርቲ ጉባኤ እና የተደረገው ጥሪ
የገዢው ብልጽግና ፓርቲ ፕሬዝዳንት እና የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ መንግሥትን በትጥቅ ለሚዋጉት የድርድር እና የንግግር፤ ለተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ደግሞ ሀገር በቀል ሀሳብ እንዲያመነጩ ጥሪ አደረጉ። "ግጭት በቃን" ሲሉ የተደመጡት የፓርቲው ፕሬዝዳንት "በእኛ በኩል በሰላም፣ በድርድር በውይይት እና በሀሳብ ለሚደረግ የፖለቲካ ትግል ግማሽ መንገድ የመሄድ" ፍላጎት እንዳለን አሳይተናል ብለዋል።
መንግሥት በኦሮሚያ ክልል ካለው ታጣቂ ቡድን ጋር ከዚህ በፊት ከሀገር ውጪ ያደረገው ድርድር አልተሳካም። በአማራ ክልል ያለውን ግጭት በሰላም ለመፍታት የአመቻችነት ሚና የወሰደው የክልሉ የሰላም ካውንስል ደግሞ "በመንግሥት እና በፋኖ መካከል አለመተማመን" በመኖሩ የሰላም የድርድር ሀሳቦች ስኬት ርቋቸዋል።
ብልጽግና ፓርቲሁለተኛ ጉባኤውን ባለፈው አርብ ሲጀምር ንግግር ያደረጉት የፓርቲው ፕሬዝዳንት ዐቢይ አሕመድ ፓርቲያቸውን መደመር የተባለ ሀገር በቀል እሳቤ ነድፎ የመጣ በሚል ሲያሞግሱ፣ ግለሰቦችም ሆነ ተቃዋሚዎች ግን ላለፉት ስድስት ዓመታት አማራጭ ሀሳብ ከማቅረብ ይልቅ "ከሳሽ" ነበሩ ሲሉ እሳቸውም ሌሎችን ከሰዋል። "ሀሳብ የለሽ ፖለቲከኞች፣ ሀሳብ የለሽ ፓርቲዎች፣ ሀሳብ የነጠፈበት አካባቢ" የሚሉ አገላለጾችን የተጠቀሙት የብልጽግና ፕሬዝዳንት "ለአጭር ጊዜ ድል የረዥም ጊዜ መከራን ያመጡብናል" ሲሉም እነዚህን በስም ለይተው ያልጠቀሷቸው አካላት ክፉኛ ወቅሰዋል።
የብልጽግና ፓርቲ ፕሬዝዳንት "አባቶቻችን" ሲሉ የጠሯቸውን አካላትም "ፖለቲካን በቅጡ አልተለማመዱም" ሲሉ ወንጅለዋል። ማሳያቸውም "ሀገርኛ ሀሳብ አላፈለቁም" የሚለው ነው። ፓርቲያቸው - ብልጽግና ለሰላም፣ ለልማት፣ ለአንድነት እጁ የተዘረጋ ስለመሆኑ ያብራሩት ዐቢይ አሕመድ ለኢትዮጵያውያን ተከታዩን መልዕክት አስተላልፈዋል።
"ግጭት በቃን። እንሰልጥን። እንነጋገር።" ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እንደ ሀገርም ሆነ እንደ ግዢው ፓርቲመሪነታቸው በልዩ ልዩ መድረኮች የሰላም፣ የድርድር ጥሪዎችን ሲያቀርቡ ይደመጣሉ። በኦሮሚያ ክልል ካለው ኦነግ ሸኔ ጋር ታንዛኒያ ድረስ ተሂዶ ከዚህ በፊት የተደረገው የድርድር ጥረት አልተሳካም። ከፋኖ ጋር ችግሮችን በሰላም ለመፍታት የተጀመረው ጥረትም ተጨባጭ ውጤት ያስገኘ አይመስልም። የአመቻችነት ሚና ይዞ የተቋቋመው የአማራ ክልል የሰላም ካውንስል የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ እያቸው ተሻለ እንደሚሉት ለዚህ ምክንያቱ በሁለቱም በኩል መተማመን መጥፋቱ ነው። ከቀኝም ከግራም በርካታ ፈተናዎች ከፊት ይጠብቁናል ያሉት የብልጽግና ፓርቲ ፕሬዝዳንት እና የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ይህንን ጨክነን እንወጣዋለን ብለዋል።
ሰለሞን ሙጬ
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሐመድ