የአውሮጳ ሃገራት ድንበራቸውን ለማላላት መዳዳታቸው
ዓርብ፣ ግንቦት 7 2012ቻይናን በመሳሰሉ ሃገራት ሁለተኛ ዙር የኮሮና ወረርሽኝ ስጋት በሆነበት በአሁኑ ጊዜ የአውሮጳ ሃገራት ድንበራቸውን ቀስ በቀስ ለመክፈት እየዳዱ ነው። የድንበር እገዳ ሲላላ የወረርሽኙ የማገርሸት ስጋት ቢኖርም በተለይ ኤኮኖሚያቸው በአመዛኙ ወደ ባህር ዳርቻዎቻቸው፣ቤተ መዘክራቸው እና ታሪካዊ ቦታዎቻቸው ከሚመጡ አገር ጎብኚዎች በሚገኝ ገንዘብ ላይ የተመሰረተው የአውሮጳ ሃገራት በበጋው የእረፍት ጊዜ ድንበር አቋራጭ ጉዞዎችን እንደገና ለመጀመር እየፈለጉ ነው። በኮሮና ወረርሽኝ ሰበብ በእጅጉ የተጎዳው የአውሮጳ ቱሪዝም እንዲያንሰራራ የአውሮጳ ህብረት 27ቱን አባል ሃገራት ሊረዳ ይችላል ያለውን እቅድ ዛሬ ይፋ አድርጓል። የህብረቱ ኮሚሽን፣ አየር መንገዶች፣መርከቦች እና አውቶብሶች የተሳፋሪዎቻቸውን እና የሠራተኞቻቸውን ደህንነት አስጠብቀው ሆቴሎችም የጤና ጥበቃ እርምጃዎች እንዲወስዱ በማድረግ ስራ የሚጀምሩበትን መንገድ እንዲያመቻቹ ፣ መንግሥታትም በተዘጉ ድንበሮች ላይ የመታወቂያ ቁጥጥርን እንዲያነሱ መክሯል።የአውሮጳ ሃገራት ምክሩን ይቀበሉ አይቀበሉ ግልጽ አይደለም።አንዳንድ የአውሮጳ ሃገራት ግን ከጎረቤቶቻቸው ጋር የሁለትዮሽ ስምምነት ላይ ለመድረስ ሞክረዋል።ኦስትሪያ እንዳለችው በጎርጎሮሳዊው የፊታችን ሰኔ 15፣2020 ከጀርመን ጋር የሚያዋስናትን ድንበር ትከፍታለች።የመታወቂያ ቁጥጥርም ከነገ ጀምሮ እንዲቀንስ ይደረጋል።የወረርሽኙ መጠን እየታየ ለጎረቤቶቿ ለስዊዘርላንድ ሊሽተንሽታይን እና ምሥራቂዊ ጎረቤቶቿ ድንበሯን እንደምታላላ አስታውቃለች። ከኢጣልያ ጋር የሚያዋስናትን ድንበሯን ለመክፈት ግን ጊዜው ገና ነው ብላለች ኦስትሪያ።ጀርመን በበኩልዋ በወደ አውሮጳ ሃገርት የሚደረግ ጉዞ ላይ የታጣለውን እገዳ እንደምታነሳ አስታውቃለች።ይህ መቼ እንደሚሆን ግን አልገለጸችም።ሆኖም ጀርመን እጅግ አስፈላጊ በማይባሉ የአገር ጎብኚዎች የውጭ ጉዞዎች ላይ እስከ ጎርጎሮሳዊው ሰኔ 14፤ 2020 ድረስ እገዳ ጥላለች።
ኂሩት መለሰ
አዜብ ታደሰ